
ገንዳውኃ፡ ጥር 16/2014 ዓ.ም (አሚኮ) በኢትዮጵያ በብዝሀ ሕይወት ሀብቱ ከፍተኛውን ድርሻ በመያዝ ይታወቃል፤ የበርሃማነት መስፋፋትና የካርቦን ልቀትን ከሚከላከሉ የሀገሪቱ ሥነ ምህዳሮች ሰፊውን ቦታ ይሸፍናል፤ በዚህም አረንጓዴ መቀነት (green belt) የሚል መጠሪያ ሥም ተሰጥቶታል– አልጣሽ ብሔራዊ ፓርክ።
የአፍሪካ ታላቁ የአረንጓዴ ምሰሶ በመባል የመታወቀው የአልጣሽ ብሔራዊ ፓርክ በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ ይገኛል። 266 ሺህ 570 ሄክታር መሬት የቆዳ ስፋት ሲኖረው በውስጡ ሊጎበኙ የሚችሉ በርካታ የተፈጥሮ መስህቦች እንዳሉት የነገራል።

የብሔራዊ ፓርኩ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኤፍሬም ወንዴ ባለ ጥቁር ጋማ ዝርያ ያለው አንበሳን ጨምሮ ከ32 በላይ አጥቢ የዱር እንስሳት ይገኛሉ። ከ130 በላይ የእጽዋት ዝርያና ከ15 በላይ የአሳ ዝርያ፣ ከ16 በላይ ተሳቢና ተራማጅ፣ ከ280 በላይ የአዋፍት ዝርያዎች መኖራቸውን ገልጸዋል።
አረንጓዴ ዘብ በመባል የሚጠራው ይህ ፓርክ የመንገድ፣ የመብራት፣ የውኃና የኔትወርክ ዝርጋታዎች ባለመሟላታቸው የቱሪስት ፍሰቱ ዝቅተኛ እንዲሆንና የአማራ ክልል ከጎብኝዎች ማግኘት የሚገባውን ገቢ እያገኘ እንዳልሆነ ነው ኃላፊው የተናገሩት።

በክረምት ወቅት ፓርኩን ገብቶ ለመጠበቅና ፍተሻ ለማድረግ አስቸጋሪ መሆኑን የገለጹት አቶ ኤፍሬም ከቱሪስቶች ገቢ ማግኘት እና በፓርኩ ውስጥ ሎጅዎች ተከፍተው ለአካባቢው ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር የሚቻለው ምቹ መንገድና ድልድይ ሲገነባ ነው ብለዋል።
የፓርኩ ሪንጄሮች (ጥበቃዎች) በበኩላቸው በሱዳን በኩል ሰርገው የሚገቡ የናይጀሪያ ፈላታ አርብቶ አደሮች የዱር እንስሳትን ለምግብነትና ለመድኃኒትነት እንዳያውሏቸው፣ ህገ ወጥ አደንና ሰደድ እሳት እንዳይፈጠር ከማድረግ ባሻገር የጠላት ኃይል ፓርኩን ምሽግ አድርጎ ጥፋት እንዳይፈጽም በንቃት እየጠበቁ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃው ባሻገር የሀገርን ድንበር እየጠበቁ መሆናቸውን የገለጹት ሪንጀሮቹ (ጥበቃዎቹ) በፓርኩ ውስጥ የንጹህ ውኃ መጠጥ፣ የኔትወርክና የመገናኛ ራዲዮ አለመኖሩ ለጥበቃ ሥራው ፈታኝ መሆኑን ተናግረዋል።

ፓርኩን በእኔ ባይነት ስሜት እየጠበቁ ያሉ ወጣቶችም በፓርኩ ውስጥ የስራ እድል እንዲፈጠርላቸውና ተጠቃሚ እንዲሆኑ መንግስት መሰረተ ልማቶችን እንዲያሟላ የአካባቢው ነዋሪዎች ጠይቀዋል።
የአማራ ክልል ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኤርሚያስ መኮንን በበኩላቸው የአልጣሽ ብሔራዊ ፓርክ ከፍተኛ የተፈጥሮ ሀብት ካላቸው የሀገሪቱ የቱሪስት መስህቦች አንዱ ቢሆንም ፓርኩን ለማልማትና ከፓርኩ የሚፈለገውን ገቢ ለማግኘት እንደ ክልል ውስንነት መኖሩን ነው የገለጹት።

ፓርኩ ተጠሪነቱ ለፌዴራል መንግስት ነው ያሉት ምክትል ኃላፊው ለጎብኝዎች ምቹ የቱሪስት መዳረሻ በማድረግ ሀገሪቱን ከቱሪዝም ሀብቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎን ለማሟላት ከፌዴራል መንግስት ጋር በመሆን በቀጣይ ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚሰራ ነው የገለጹት።
ዘጋቢ:–ቴዎድሮስ ደሴ–ቋራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ቲክቶክ tiktok.com @amharamediacorporation
በአሸባሪውና ወራሪው የትግራይ ቡድን በዋግኽምራና በወሎ አካባቢዎች የወደሙና የተዘረፉ የሚዲያ መሳሪያዎችን መልሶ በመገንባት ለሕዝብ አገልግሎት ለመስጠት አሚኮን ይደግፉ።