
ባሕር ዳር፡ ታኅሣሥ 11/2014 ዓ.ም (አሚኮ) የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዲኤታ ሰላማዊት ካሳ በቱርክ ኢስታንቡል በተካሄደው የቱርክ አፍሪካ ጉባኤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) የተመራዉ የልዑካን ቡድን የተሳካ ተሳትፎ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡
‘የተጠናከረ አጋርነት ለጋራ እድገትና ብልጽግና’ በሚል ሐሳብ በተካሄደው በዚህ ጉባኤ ቱርክ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ያላትን ሁለንተናዊ እድገት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መምከሩንም ተናግረዋል፡፡
አፍሪካ በዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ያላትን ውክልና ማሳደግ እንደሚገባት በጉባኤው ሐሳቦች መነሳታቸውን ጠቅሰዋል፡፡
ቱርክ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር በተለያዩ መስኮች በትብብር እየሠራች መሆኑን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታዋ በጉባኤውም የጋራ ተጠቃሚነት ላይ ያተኮሩ ትብብሮች እንደሚያስፈልጉም መገለጹን አመላክተዋል፡፡
ከጉባኤው ጎን ለጎን ኢትዮጵያና ቱርክ ትብብራቸውን ማጠናከር የሚያስችሉ የሁለትዮሽ ምክክሮችን በማድረግ የልዑካን ቡድኑ የተሳካ ቆይታ አድርጓል ብለዋል፡፡
#ተነሳ!!
#መሪህን ተከተል!!
#ሀገርህን አድን!!
#ነፃነትህን አትስጥ !!
#አካባቢህን ጠብቅ!!
