
ሕዳር 24/2014 ዓ.ም (አሚኮ)ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን፣ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች ወደ ሀገር ቤት በመግባት በዓላቶችን እንዲያከብሩ ጥሪ ማቅረባቸው ይታወቃል።
የአውሮፓዊያኑን አዲስ ዓመት በኢትዮጵያ ለማክበር 1 ሚሊዮን ዲያስፖራዎች ወደ ሀገር ቤት እንዲገቡ የቀረበውን ጥሪ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ የተግባር ምክር ቤት አጋር ኾኖ ለማስተባበር ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ዳያስፖራ የተግባር ምክር ቤት እንዳስታወቀው፤ የቀረበውን ግብዣ በመደገፍ ለተግባራዊነቱ አብሮ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጧል።
ዳያስፖራው ወደ ሀገር ውስጥ በመግባት የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ለማሳደግና ለማዘመን የራሱን ዐሻራ እንዲያስቀምጥ ለማድረግ ወሳኝ መሆኑን ምክር ቤቱ አመልክቷል።
አሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን ከውጭ ጠላቶች ጋር በመቀናጀት ሀገር ለማፍረስ የከፈተውን ጦርነት ለመቀልበስና ሀገር ለማዳን በሚደረገው ትግል በመሳተፍ የቀረበውን ጥሪ በመቀበል አጋር ኾኖ ለማስተባበር ዝግጁ እንደሆነም አመልክቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በአውደ ግንባር እየመሩት ባለው “ዘመቻ ለኅብረ ብሔራዊ አንድነት” የኢትዮጵያ አሸናፊነት ይረጋገጣል ያለው የምክር ቤቱ መግለጫ፤ በሠራዊቱ የጀግንነት ተጋድሎና ድል መኩራቱን ገልጿል።
ዳያስፖራው በሚገኝባቸው ሀገራት ኹሉ በሰላማዊ ሰልፍና በዲፕሎማሲ ዘመቻ የዜግነት ድርሻውን በመወጣት ከመንግሥት ጎን መሆኑን እያሳየ መሆኑን ጠቅሷል፡፡
በኢትዮጵያ ላይ የተደቀነውን የኅልውና አደጋ ለመቀልበስና ሰላም ለማረጋገጥ የመንግሥትን ጥሪ ተቀብሎ ዳያስፖራው ወደ ሀገሩ እንዲገባ ጥሪ አቅርቧል።
በመጪው ታኅሣሥ 29/2014 ዓ.ም 1 ሚሊየን ሰዎች ወደ ሀገር ቤት እንዲገቡ በመንግሥት በኩል ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝ ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ቲክቶክ tiktok.com @amharamediacorporation