
ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 22/2014 ዓ.ም (አሚኮ) አሸባሪውና ወራሪው የትህነግ ቡድን ኢትዮጵያን ለማፈራርስ ቆርጦ መነሳቱን ተከትሎ የአማራ ክልል መስተዳደር ምክር ቤት ትላንት ባካሄደው 6ኛ ዙር፣ 1ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ አስቸኳይ ስብሰባ ለሕዝቡ የክተት ጥሪ አስተላልፏል፡፡
የቀረበውን የክተት ጥሪ ተከትሎም ሕዝቡ ከተለያዩ አካባቢዎች ወደ ግንባር እየተመመ ነው፡፡ የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ነዋሪዎችም ለጥሪው ፈጣን ምላሽ በመስጠት ወደ ግንባር ለመዝመት መዘጋጀታቸውን የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዋና አስተዳዳሪ እንግዳ ዳኛው ተናግረዋል፡፡
የብሔረሰብ አስተዳደሩ ነዋሪዎች የሽብርተኛው ትህነግ ወራሪ ቡድን አማራን ለማጥፋት አሰፍስፎ የተነሳ መሆኑን በመረዳት በግንባር ለመፋለም ሁሉም መዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡
የሽብርተኛው ትህነግ ተላላኪዎችን ለመመከት በግንባር የማይሳተፈው ኅብረተሰብም አካባቢውን በንቃት እየጠበቀ መሆኑን አቶ እንግዳ ገልጸዋል፡፡
በየደረጃው ያሉ የሥራ ኀላፊዎችም ሕዝብን በማደራጀት አሰፈላጊውን ሁሉ በማድረግ ታሪካዊ ኀላፊነት እየተወጡ መሆኑን አስታውቀዋል::
ዘጋቢ፡- አዳሙ ሽባባው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ