
ባሕር ዳር፡ መስከረም 28/2014 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮጵያና የሕዝቦቿ ጠላቶችና ተባባሪዎቻቸው ከውስጥና ከውጭ ሆነው የሳይበር ምህዳሩን በመጠቀም በተለያዩ የመሰረተ ልማትና የመረጃ አውታሮች ላይ ቀጥተኛ ጥቃት ለመፈጸም እያደረጉት ያለው ሙከራ አለመሳካቱን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ አስታውቋል፡፡
ኢትዮጵያ እያከናወነች ባለችው ከህግ ማስከበርና የህልዉና ዘመቻ ጋር እንዲሁም ሌሎች ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታዎች ጋር በተያያዘ በሳይበር ምህዳሩ ላይ እየታዩ ያሉት አዝማሚያዎችና ሙከራዎቻቸውን ማሳሰብና ማሳውቅ አስፈልጓል ብሏል ኤጀንሲው፡፡
እነዚህ እኩይ ዓላማ ያላቸው አካላት ሀገር ዉስጥ ሆነው የመሰረተ-ልማትና የመረጃ አውታሮችን እንዲሁም ሲስተሞችን እንዲያስተዳድሩ በተቋማት መብት የተሰጣቸውን (ሲስተም አድሚኒስ) ለሙያቸው፣ ለተቋማቸውና ለሀገራቸው ታማኝ ያልሆኑ ጥቂት ጡት ነካሽ ባንዳዎችን በመጠቀምና እክል ለመፍጠር እየሰሩ ነው ብሏል፡፡
ማንኛዉንም የመሰረተ ልማትና የመረጃ አውታሮችን እንዲሁም ሲስተሞችን የምታስተዳደሩ መንግሥታዊም ሆነ መንግሥታዊ ያልሆናችሁ ተቋማት፣ ሲስተሞችን እንዲያስተዳድሩ መብት የተሰጣቸው ወይም የተቋማትን የማኅበራዊ ሚዲያ አካውንቶችን እንዲያስተዳድሩ የይለፍ-ቃል (ፓስወርድ) እንዲይዙ የተፈቀደላቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ወይም (ሲስተም ወይም ኔትወርክ አድሚንስ) ትክክለኛውን የሙያ ብቃት እና ጥብቅ የሥነ ምግባር ማጣራት የተደረገባቸው መሆኑን ደጋግማችሁ እንድታረጋግጡ ሲል ማሳሰቡን ከኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ