
ባሕር ዳር፡ መስከረም 12/2014 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ሕንፃ ሥራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅት ለሕልውና ዘመቻው በዓይነትና በገንዘብ 45 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል። የአማራ ሕንፃ ሥራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ቢያዝን እንኳሆነ ድጋፉ ከሠራተኛው የወር ደመወዝ፣ በድርጅቱ ውስጥ ካሉ ሲቪክ አደረጃጀቶች ማለትም ከሠራተኛ መሰረታዊ ማኅበር፣ ከሠራተኛው መረዳጃ ማኅበር እና ከሠራተኛ ገንዘብ እና ቁጠባ ማኅበር የተሰበሰበ ነው ብለዋል።
ሥራ አስፈፃሚው ከ4 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ችግር ላይ በመሆኑ ሁሉም ሰው የሚችለውን ድጋፍ ሊያደርግ ይገባል ብለዋል። ድጋፉ በሽብርተኛው ትህነግ ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ ዜጎች እና የሽብርተኛው ትህነግን ወራሪ ቡድን በግንባር እየተፋለመ ላለው የፀጥታ ኀይል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
ዋና ሥራ አስፈፃሚው እንዳሉት ድርጅቱ እንደ ተቋም ከ17 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ጥሩ ብርሃን ፖሊስ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩትን በመገንባት የስልጠና ተግባሩን እንዲጀምር እና የመጀመሪያ ዙር ስልጣኞችን እንዲያስመርቅ አድርጓል፡፡ በግንባር ለህልውና ዘመቻው እየተዋደቀ ለሚገኘው የሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ ለልዩ ኃይል፣ ሚሊሻ እና ፋኖ የሚሆን 20 ኩንታል በሶ እና ሁለት ኩንታል ደረቅ ምግብ ተዘጋጅቶ ድጋፍ መደረጉንም ጠቅሰዋል፡፡
ከ75 በላይ የድርጅቱ የሥራ ኀላፊዎችና ሠራተኞች እንዲሁም ከ34 በላይ የሚሆኑ የድርጅቱ ከባድና ቀላል ተሽከርካሪዎችና ማሽኖች ወደ ግንባር ተሰማርተው የሚፈለገውን ድጋፍ እየሰጡ መሆናቸውን ሥራ አስፈፃሚው ተናግረዋል።
ሠራተኞችም ለሕልውና ዘመቻው ገንዘብ መስጠት ብቻ ሳይሆን እስከ ሕይወት መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ከ80 በላይ ሠራተኞች የተጠባባቂ ኃይል ስልጠና ወስደው ሲመረቁና ደም ሲለግሱም አማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ተመልክቷል
ዘጋቢ፦ አዳሙ ሽባባው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ