አሸባሪውና ወራሪው የትህነግ ቡድን የአቅመ ደካሞችን ቀለብ ሳይቀር ዘረፋ መፈጸሙን የገረገራ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ።

340
መስከረም 04/2014 ዓ.ም (አሚኮ) አሸባሪውና ወራሪው የትህነግ ቡድን በሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ በአማራ ክልል ልዩ ኃይል፣ ሚሊሻ፣ ፋኖና በአካባቢው ማኅበረሰብ ከደቡብ ጎንደር ዞን ጋሳይ ከተማ ጀምሮ እየተቀጠቀጠ እስከ ሰሜን ወሎ ዞን ጋሸና ከተማ ደርሷል።
ቡድኑ በደቡብ ጎንደር ዞን ከሚገኙ የጋሳይ፣ ክምር ድንጋይ፣ ጎብጎብ፣ ነፋስ መውጫና ሌሎችም አካባቢዎች ተጠራርጎ እስኪወጣ ድረስ ግድያ፣ አስገድዶ መድፈር መጠነ ሠፊ ዘረፋና ውድመት ማድረጉን የአሚኮ ጋዜጠኞች ቡድን በስፍራው ተገኝቶ መዘገቡ ይታወሳል።
አሁንም የሽብር ቡድኑ በደረሰበት ጭፍጨፋ በሰሜን ወሎ ዞን መቄት ወረዳ የሚገኙ ደብረ ዘቢጥ፣ ኮኪት፣ አግሪት፣ ፍላቂትና ገረገራን ለመልቀቅ ተገዷል።
ቡድኑ እንደልማዱ በእነዚህ አካባቢዎችም የሚያደርሰውን ውድመት ቀጥሎበታል። የፍላቂት ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት ጎበዜ በዛብህ አሸባሪው ቡድን በከተማዋ ውስጥ ባደረገው ቆይታ “የሚበላ አምጣ” በማለት ኅብረተሰቡን ሲያስቸግር እንደቆየ ተናግሯል። ቡድኑ ጉልበቱን በመጠቀም የሚበላና የሚጠጣ ሲቀማ እንደቆየ ነው ወጣቱ የተናገረው።
ሌላው የፍላቂት ከተማ ነዋሪ አገኘሁ ምስጋን አሸባሪው ቡድን በከተማዋ ባደረገው የወረራ ቆይታ የነዋሪዎች ኪስ በመግባት ገንዘብና የተገኘውን ቁሳቁስ ሁሉ ወስዷል ብሏል። “ገንዘብ አምጡ እያሉ ቤታችንን ይደበድቡታል፣ ንፁሕ አየር መተንፈስ የቻልነው የወገን ኃይል ሲደርስልን ነው” ብሏል።
የገረገራ ከተማ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ገነት አበባው አሸባሪው ቡድን በከተማዋ ውስጥ ባደረገው ቆይታ የቤት አስቤዛዎችን ጠራርጎ በመውሰድ ኅብረተሰቡን የሚበላ እንዳሳጡት ተናግረዋል።
ሌላው የገረገራ ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት አበባው ሙጬ “አሸባሪውና ወራሪው ትህነግ ብልጽግና ምንድነው፣ ብልጽግናን ለምን መረጣችሁት” በማለት ኅብረተሰቡን ሲያንገላታ እንደቆየ አስረድቷል። አሸባሪው ቡድንም በደረሰበት ከባድ ጥቃት ከተማቸውን ለቆ እንደወጣ ተናግሯል።
የአሚኮ የጋዜጠኞች ቡድም ገረገራ ከተማ በመገኘት ኅብረተሰቡ ከሽብር ቡድኑ ነፃ ከወጣ በኋላ የተሰማውን ደስታ ለመመልከት ችሏል።
ዘጋቢ:- ቡሩክ ተሾመ- ከገረገራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous articleበእስራኤል የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለህልውና ዘመቻ ከ340 ሺህ ብር በላይ ድጋፍ አደረጉ፡፡
Next articleአሸባሪው የትህነግ ወራሪ ቡድን ወረራ በፈፀመባቸው የሰሜን ወሎ የተለያዩ አካባቢዎች ዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅቶች የሰብዓዊ ድጋፎችን እንዲያቀርቡ ከዞኑ የተፈናቀሉ ወገኖች ጠየቁ።