
ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 21/2013 ዓ.ም (አሚኮ) የደሴ ከተማ ለጠላቶቿ የእግር እሳት መሆኗን ከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል፡፡ የደሴ ከተማ በአሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን ከተለያዩ አካባቢወች የተፈናቀሉ ወገኖቿን አቅፋ መያዟንም ነው አስተዳደሩ የገለጸው፡፡
ከተማዋ በአሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን የተፈናቀሉ 107 ሺህ ሰዎችን ተቀብላ አለኝታነቷን እያሳየች እንደሆነ የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ አቶ ሰይድ የሱፍ ነግረውናል። ምክትል ከንቲባው እንግዳ ተቀባዩ የደሴ ሕዝብ እስካሁን ድረስ 20 ሚሊዮን የሚገመት የአይነትና የገንዘብ ድጋፍ ለተፈናቃዮች አዋጥቷል ብለዋል።
ከተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማት 15 ሺህ ኩንታል እህል መገኘቱንም ነው የገለጹት።
የደሴ ሕዝብ ተፈናቃይ ወገኖቹን ከመርዳት ባለፈ አሸባሪውን የትግራይ ወራሪ ቡድን ለመቅበር ዝግጁ እንደሆነም አስረድተዋል። አሸባሪ ቡድኑ አስርጎ ያስገባቸውን 300 ተጠርጣሪዎች ሕዝቡ በቁጥጥር ስር አውሏል፤ እስካሁን በተደረገው ምርመራ 8ቱ በቀጥታ ከአሸባሪው ቡድን ተልእኮ የተሰጣቸው እንደሆኑ ተረጋግጧል፤ ቀሪዎቹ ደግሞ በምርመራ ላይ እንደሚገኙ ነው ምክትል ከንቲባው ያብራሩት።
ዘጋቢ፡-ሰለሞን አንዳርጌ-ከደሴ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ