
ርእሰ መሥተዳድሩ በክምር ድንጋይ 11 የአሸባሪው ትህነግ አባላት የረፈረፉትን አቶ ጌጤ መኳንንትን አግኝተው አበረታተዋል።
ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 17/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በደቡብ ጎንደር ዞን ጉና ቤጌምድር ወረዳ ክምር ድንጋይ ከተማ ያፈራቻቸው የወቅቱ ጀግና ናቸው አቶ ጌጤ መኳንንት-አባ ረፍርፍ፡፡ አሸባሪው ትህነግ በደቡብ ጎንደር ዞን ክምር ድንጋይ አካባቢ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጥቃት ሲያደርስ አቶ ጌጤ ለሕዝባቸው መስዋእት መሆን እንደሚገባ ቀድመው ራሳቸውን አሳምነዋል። የሽብር ቡድኑ አባላት ከሆቴላቸው ገብተው በቀጭን ትእዛዝ የሚፈልጉትን ሲያስቀርቡ አባ ረፍርፍ 11ዱን እስከወዲያኛው በመሸኘት ወደ ጫካ ገብተው አኩሪ ጀብድ ፈጽመዋል። የዘመናችን የአማራ ሕዝብ ማንነትና አኩሪ ታሪክ አንዱ ማሳያ የሆኑት አቶ ጌጤን የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አገኘሁ ተሻገር አግኝተው አበረታተዋቸዋል።
አቶ ጌጤ አሸባሪው ትህነግ የአማራን ሕዝብ ማንበርከክ እንደማይችል እኔ ህያው ምስክር ነኝ ብለዋል።
አሸባሪው ትህነግ ወረራ በፈጸመባቸው የአማራ ክልል አካባቢዎች ዘረፋና ጥቃት እየፈጸመ ሲመጣ ሕዝባችን ኢትዮጵያን ለማዳን ከተሰለፈው ሠራዊት ጋር ተባብሮ ታግሏል፤ ብዙ ጀግኖችንም አይተናል ያሉት ደግሞ የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አገኘሁ ተሻገር ናቸው።
አቶ ጌጤን ጨምሮ ለአማራ ሕዝብና ለኢትዮጵያ ህልውና እየተዋደቁ ላሉ ጀግኖች መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ርእሰ መሥተዳድሩ አረጋግጠዋል። የሽብር ቡድኑ ዓላማ ሕዝባችንን በማንበርከክ ኢትዮጵያን ማፍረስ በመሆኑ ህልውናውን እስከማክሰም የሚደርስ ትግላችን ይቀጥላል፤ የአማራ ሕዝብም እያሳዬ ያለውን አኩሪ ድጋፍ አጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።
ዘጋቢ፡- ስማቸው እሸቴ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ