
ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 12/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በአውስትራሊያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የህልውና ዘመቻን መደገፍ በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ ውይይት በማካሄድ ድጋፍ አድርገዋል።
በአውስትራሊያ የኢፌዴሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለ ሙሉ ስልጣን አምባሳደር ዶክተር ሙክታር ከድር አሸባሪው የትህነግ ቡድን የተናጠል ተኩስ አቁም ውሳኔ ባለመቀበል ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በመተሳሰር ኀይሉን አሰባስቦ ሕጻናትን ለጦርነት በአማራና አፋር ክልሎች ላይ ወረራ መፈጸሙን ተናግረዋል። በዚህም መከላከያ ሠራዊት በአሸባሪው ቡድን ላይ እርምጃ በመውሰድ የሀገሪቱን ህልውና ለማስጠበቅ አስፈላጊውን ሁሉ እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎች ዳያስፖራው በቀላሉ ገንዘብ እንዲልክና የህልውና ዘመቻውን ሊያግዝ የሚችልባቸው ተጨማሪ የኦንላይን ማስተላለፊያ ይፋዊ መንገዶች እንዲመቻች ጠይቀዋል፡፡
በዳያስፖራ አደረጃጀቶች የሚያሰባስቡት ድጋፍ እንደተጠበቀ ሆኖ በዕለቱ ከተገኙ ተሳታፊዎች 25 ሺህ የአውስትራሊያ ዶላር መከላከያ ሠራዊት ለመደገፍ ቃል ተገብቷል፡፡ በርካታ ተሳታፊዎች በየወሩ ከ100 እስከ 300 ዶላር ለአንድ ዓመት ጊዜ በቋሚነት ለመለገስ ቃል እንደገቡ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል ዐቀባይ ጽሕፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያመላክታል፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ