
ባሕር ዳር: ነሐሴ 04/2013 ዓ.ም (አሚኮ) አሸባሪውን ትህነግ ለመደምሰስ እየተደረገ ባለው የህልውና ዘመቻ የንፋስ መውጫ ነዋሪዎች ለመከላከያ ሠራዊት፣ ለልዩ ኀይል፣ ለሚሊሻ እና ለፋኖ ድጋፍ እያደረጉ ይገኛል፡፡ ነዋሪዎቹ የስንቅ እና ሌሎች አስፈላጊ ቁሳቁሶችን በማሰባሰብ ወደ ግንባር በመላክ ላይ እንደሚገኙም ተመልክቷል፡፡

የንፋስ መውጫ ከተማ የድጋፍ አሰባሳቢ ኮሚቴ አስተባባሪ አቶ ያሬድ አለነ ከኀብረተሰቡ ውስጥ ድጋፍ አሰባሳቢ፣ አዘጋጅ፣ አቅራቢ እና መጋቢ ኮሚቴዎች ተዋቅረው በተጠናከረ እና በተቀናጀ መልኩ ለሠራዊቱ እያደረሱ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቂ አቅርቦትም አለ ብለዋል፡፡ ኀብረተሰቡ ባለው አቅም ልክ የትግሉ ተሳታፊ ኾኗል ያሉት አቶ ያሬድ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚጠብቀውን ውጤት ለማምጣት አጋዥ እንደሚኾን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡

ወይዘሪት አስካል አሰፋ ለሠራዊቱ ስንቅ ከሚያዘጋጁ ወጣቶች መካከል አንዷ ናት፡፡ የከተማውን እና አካባቢውን ማኀበረሰብ በማስተባበር በተጠናከረ ሁኔታ ስንቅ እና ሌሎች ድጋፎችን ለመከላከያ ሠራዊት፣ ለልዩ ኀይል፣ ለሚሊሻ እና ለፋኖ እያቀረቡ መሆኑን ተናግራለች፡፡
ወጣት አበበ ያለምነው በበኩሉ “ገንዘብ ያለው በገንዘቡ፣ጉልበት ያለው በጉልበቱ ከዳር ዳር ተነቃንቆ ለሠራዊቱ ድጋፍ እያደረገ ነው” ብሏል፡፡
ዘጋቢ፡- ቢኒያም መስፍን-ከንፋስ መውጫ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ