
ኅብረተሰቡ ከማደናገሪያ አሉባልታዎች ራሱን ሊጠብቅ እንደሚገባ የሰሜን ጎንደር ዞን ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት አሳሰበ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 30/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በአሁኑ ወቅት አሸባሪው የትህነግ ቡድን የውስጥና የውጭ ባንዳዎችን በመጠቀም የውሸት ፕሮፖጋንዳ እያሰራጨ መሆኑን ማኅበረሰቡ ሊገነዘብ እንደሚገባ የሰሜን ጎንደር ዞን ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት አሳስቧል።
በጽሕፈት ቤቱ የሚሊሻ ስምሪት ባለሙያ ዐቢይ ደርበው እንደገለጹት የሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ ልዩ ኀይል፣ ሚሊሻና ፋኖ አሸባሪው የትህነግ ቡድን ላይ እርምጃ እየወሰዱ ነው። ይህ የዘመቻ ተግባር እየተከናወነ በሚገኝበት ባሁኑ ወቅት ደግሞ አንዳንድ ግለሰቦች ተጨባጭ ያልሆነ አሉቧልታ ሲያወሩ ይደመጣሉ ያሉት አቶ ዐቢይ ማኅበረሰቡም ከእንደነዚህ ዓይነት አሉቧልተኞች ራሱን ሊያጸዳ ይገባል ብለዋል፡፡ ያልተረጋገጠ ወሬ የሚያስወሩ ሰዎችም ከድርጊታቸው ሊታቀቡ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት፡፡
ሚሊሻው በአሁኑ ወቅት ከሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ ከልዩ ኀይል እና ከፋኖ ጋር በመሆን የጠላት የእግር እሳት መሆኑንም አስረድተዋል።
ወጣቶች ስልጠና ወስደው ለዘመቻው ዝግጁ እንደሆኑም ተናግረዋል።
በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጭ ያሉ ሀገር ወዳድ ዜጎችም በማኅበራዊ የትስስር ገጽና በተለያየ መንገድ ከሚሰራጨው የሐሰት ወሬ በመራቅ ከታማኝ ምንጮች መረጃ መውሰድ እንዳለባቸውም ነው ያስገነዘቡት።
ኅብረተሰቡ ከጸጥታ ኀይሎች ጎን በመሠለፍ አስፈላጊውን እገዛ ማድረግ እንደሚጠበቅበትም አስገንዝበዋል።
ዘጋቢ:- አዳሙ ሽባባው -ከደባርቅ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
