
አሸባሪው ትህነግ በወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ላይ የፈጸመውን ግፍ አስመልክቶ ያካሄደውን የጥናት ውጤት ለሕዝብ ይፋ ለማድረግ እየሠራ መኾኑን የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ገለጸ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 29/2013 ዓ.ም (አሚኮ) አሸባሪው ትህነግ ባለፉት ዓመታት በወልቃይት፣ በጠገዴ እና በጠለምት ሕዝብ ላይ የፈጸመውን በደል አስመልክቶ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ያካሄደውን ጥናት ውጤት ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለማቅረብ እየሠራ እንደሚገኝ በዩኒቨርሲቲው የጥናቱ ቡድን መሪ ረዳት ፕሮፌሰር ጌታ አስራደ ነግረውናል፡፡
ረዳት ፕሮፌሰሩ እንዳሉት አሸባሪው ትህነግ ባለፉት አርባ ዓመታት በወልቃይት፣ በጠገዴ እና በጠለምት የአማራ ሕዝብ ላይ ያደረሰውን ግፍ የሚያሳይ አምስት ክፍሎች ያሉት ጥናት ተካሂዷል፡፡
በመጀመሪያው ክፍል የወልቃይት፣ የጠገዴ እና የጠለምት ሕዝብ ታሪክ፣ ማንነት እና ባሕል በአሸባሪው ትህነግ በኀይል በቁጥጥር ስር ከመውደቃቸው በፊት ያለው ሁኔታ ተዳስሶበታል፡፡
በሁለተኛው ክፍል ደግሞ አሸባሪው ትህነግ በእነዚህ አካባቢዎች የፈጸመው የዘር ፍጅት እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት የተመለከተ ነው፡፡
ከጤና እና ከትምህርት አኳያ የደረሱ በደሎች ደግሞ በሦስተኛው ክፍል መዳሰሱን የጥናቱ ቡድን መሪው ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ በአካባቢው የተፈጸመው የምጣኔ ሀብት ምዝበራ እና ኢ-ፍትሐዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር የተመላከተበት ሲኾን የዘር ተኮር ጥቃቱን እና የሚዲያ ተሳትፎ ምን እንደሚመስል መካተቱንም አንስተዋል፡፡
ሙሉ የጥናቱ ውጤት በቀጣይ በሰነድ፣ በመጽሐፍ እና በተለያዩ ሚዲያዎች ተዘጋጅቶ ለሀገር ውስጥ እና ለዓለም ዓቀፍ ማኅበረሰብ እውነታው ይፋ እንደሚኾን ነግረውናል፡፡ ይህም ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እውነታውን እንዲረዳ ያግዛል ተብሏል፡፡
ጥናቱ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ጭምር እየተዘጋጀ መኾኑንም ረዳት ፕሮፌሰሩ ገልጸዋል፡፡
አሸባሪው ትህነግ በማይካድራ ከ1 ሺህ 500 በላይ ሰዎችን ጨፍጭፏል።
ዘጋቢ፡- ዳግማዊ ተሠራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2RnNHCq
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m
