
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለሕልውና ዘመቻው የሚውል ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ በዓይነት ድጋፍ ለአማራ ክልል አስረከበ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 22/2013 ዓ.ም (አሚኮ) አሸባሪው የትህነግ ቡድን በኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊ አንድነት ላይ የቃጣውን የሽብር ተግባር ለመመከት የሚደረገው ድጋፍ በአራቱም አቅጣጫ እንደቀጠለ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለሕልውና ዘመቻው የሚያደርገው ድጋፍ በአራት አቅጣጫ የተመራ መሆኑንም የከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል፡፡ ለሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ ለአፋር ክልል እና በአማራ ክልል በጎንደር እና በኮምቦልቻ በኩል እንዲደርስ እየተደረገ ነውም ተብሏል፡፡
በጎንደር በኩል ላለው የሕልውና ዘመቻ በግንባር የተደረገውን የከተማ አስተዳደሩን ድጋፍ ያስረከቡት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት መምሪያ ኅላፊ አቶ ዘላለም ሙላት ናቸው፡፡ በዓይነት የተደረገው ድጋፍ ከከተማ አስተዳደሩ ባለሃብቶች እና ነዋሪዎች የተሰበሰበ መሆኑንም አቶ ዘላለም ገልጸዋል፡፡ 139 ሰንጋ፣ 1 ሺህ 809 በግና ፍየል፣ በኹለት መኪና የተጫነ ብስኩት፣ 121 ኩንታል ጤፍ፣ በሶ፣ ማካሮኒ፣ በቆሎ፣ ሩዝ፣ ምስር፣ ክክ እና ሌሎች አስፈላጊ ምግብነክ ቁሳቁስ ናቸው ተብሏል፡፡
ድጋፉ ለሀገር ሕልውና ዘብ ለቆመው ኅይል የሚያንስበት እንጂ የሚበዛ አይደለም ያሉት የልዑኩ መሪ የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና ነዋሪዎቿም ዘመቻው በድል እስኪጠናቀቅ ድረስ አጋርነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያደረገውን ድጋፍ የተረከቡት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማኅበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ እና የአማራ ክልል ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኅላፊ ሙሉነሽ አበበ (ዶ.ር) “አዲስ አበባ የኢትዮጵያውያን መዲናነቷን በተግባር ስታረጋግጥ ይህ ድጋፍ የመጀመሪያዋ አይደለም” ብለዋል፡፡
የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት፣ ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም አሸባሪው ቡድን በአማራ ክልል ላይ በሰነዘረው ጥቃት ለተጎጂዎች ድጋፍ በማድረግ እና በክልሉ የነበሩ ተፈናቃዮችን በመደገፍ አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቀዳሚ እንደነበረች ለአብነት አንስተዋል፡፡
ወቅቱ የተልዕኮ ጦርነት ከከፈቱብን ቡድኖች ጋር የሕልውና ዘመቻ የምናደርግበት ወቅት መሆኑን ዶክተር ሙሉነሽ ገልጸዋል፡፡
የአማራ እና የአፋር ክልሎች ፊት ለፊት የተገኙ እና የችግሩ ግንባር ቀደም ገፈት ቀማሽ ቢያስመስላቸውም አሸባሪው ቡድን የሁሉም ኢትዮጵያዊ የሕልውና ስጋት መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ ሁሉም ብሔር ብሔረሰቦች በሁሉም አቅጣጫ የሚያደርጉት ድጋፍ እና ተነሳሽነት ለኢትዮጵያ ትንሳኤ ተስፋ ሰጭ ነው ብለዋል ዶክተር ሙሉነሽ፡፡
በኢትዮጵያ ፈተና ወቅት ሕዝብን እየመሩ ከፊት መገኘት ኩራት ብቻ ሳይሆን መታደልም እንደሆነ ነው ዶክተር ሙሉነሽ አበበ የገለጹት፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ላደረገው ድጋፍ እና ላሳየው አጋርነት የአማራ ክልል መንግሥት እውቅና ይሰጣል ብለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ልዑክ ድጋፉ በተጓጓዘባቸው አካባቢዎች ሕዝቡ ላሳየው አብሮነት እና የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ላደረገላቸው አቀባበል ምሥጋና አቅርበዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ታዘብ አራጋው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2RnNHCq
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m
