
ለአሸባሪው ሕወሓት ቡድን በተለያየ መንገድ ድጋፍ ሲያደርጉ የነበሩ 28 ግለሰቦችና ንብረቶቻቸው በቁጥጥር ስር ማዋሉን የሶማሌ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 15/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በሶማሌ ክልል የሚገኙ የጁንታው ተላላኪዎች ለቡድኑ የተለያዩ ድጋፎችን ሲያደርጉ መቆየታቸውን የገለፁት የሶማሌ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ረዳት ኮሚሽነር መሐመድ አሊ ሐሰን 28 ግለሰቦች፣ 10 የሲኖትራክ መኪና እና ሌሎች ንብረቶቻቸው በኅብረተሰቡ ጥቆማና በፖሊስ በተደረገ ከፍተኛ ክትትል መያዛቸውን አስታውቀዋል።
ግለሰቦቹ በክልሉ ብጥብጥ ለማስነሳት አቅደው ሲንቀሳቀሱ መቆየታቸውንም ነው ረዳት ኮሚሽነሩ የገለፁት። ለዚህ ተግባር እንዲያብሩ ከዚህ ቀደም የነበረው አመራር አባላትና ደጋፊዎች የሆኑ የክልሉ ተወላጆችን በማስተባበር ሲሠሩ ቆይተዋልም ብለዋል ረዳት ኮሚሽነሩ።
በተለይ የሶማሌ ክልል ልዩ ኃይል ፖሊስ ለሀገራዊ ጥሪ ምላሽ ለመስጠት ወደ ግዳጅ ማምራቱን ተከትሎ በክልሉ የሚገኙ የጁንታው ተላላኪዎች ይህንን ሀገራዊ ኀላፊነት ሌላ ቅጥያ ስም በመስጠትና በማኅበራዊ ሚዲያ ለፕሮፖጋንዳነት በመጠቀም ሂደቱን ለማስተጓጎል ሲጥሩ ነበርም ብለዋል።
የክልሉ ልዩ ሃይል ፖሊስ የሀገሪቷን ሉዓላዊነት እና ሕገ መንግሥት ለመጠበቅ የገባውን ቃለ መሀላ ለመተግበር ዛሬም ኾነ ነገ ዝግጁ ነው ያሉት ረዳት ኮሚሽነሩ ጁንታው ሥርዓተ ቀብሩ እስኪፈፀም ድረስም ድጋፋችን ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት።
ለጁንታው ድጋፍ እያደረጉ የሚገኙ ግለሰቦችና በማኅበራዊ ሚዲያ የተለያዩ ሐሰተኛ መረጃዎችን በማሰራጨትና ንብረቶቻቸውን በመሸሸግ እየተባበሩ የሚገኙ የክልሉ ተወላጆች ከዚህ ተግባራቸው እንዲቆጠቡ ረዳትኮሚሽነሩ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። ከዚህ በኋላ በእንደዚህ አይነት ተግባር ውስጥ የተገኘ ግለሰብም ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድበት ነው መግለጻቸውን ኢብኮ ዘግቧል፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2RnNHCq
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m