
የሰላምን ዋጋ በመረዳት ለሀገር ሰላም ሁሉም ዘብ እንዲቆም የደባርቅ ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ጥሪ አቀረበ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 13/2013 ዓ.ም (አሚኮ) 1 ሽህ 442ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል በደባርቅ ከተማ በድምቀት ተከብሯል፡፡ የደባርቅ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ መልካሙ አቡሐይ በበዓሉ የኢድ ሶላት ሥነ ሥርዓት ላይ ተገኝተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ለህልውና ዘመቻው ሕዝበ ሙስሊሙ እያደረገ ላለው የጎላ አስተዋጽኦም ምስጋናም አቅርበዋል፡፡ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል፡፡
የደባርቅ ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ጸሐፊ ካሳ እስማኤል 1 ሽህ 442ኛው የአረፋ በዓል ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫና የህዳሴው ግድብ ኹለተኛ ዙር የውኃ ሙሌት በሰላም መጠናቀቅ በኋላ የሚከበር በዓል መሆኑ የበለጠ ደስታ የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል፡፡

“ኅብረተሰቡ በዓሉን በሰላም እንዲያከብርና በሰላም ወጥቶ በሰላም እንዲገባ ሰላም ያስፈልጋል” ብለዋል ጸሐፊ፡፡ የሰላምን ዋጋ በመረዳት ለሀገር ሰላም ሁሉም ዘብ እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በበዓሉ ላይ አሚኮ ያነጋገራቸው የደባርቅ ከተማ ነዋሪ እርዚቅ አሊ በሽር ለህልውና ዘመቻው የገንዘብ፣ የቁሳቁስ፣ የዕለት ቀለብ በማዋጣት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
አቶ እርዚቅ በግንባር ተሰልፈው የትህነግ አሸባሪ ቡድንን ለመዋጋት ዝግጁ ነኝ ብለዋል፡፡
በዓሉ በተክቢራ ተጀምሮ የኢድ ሶላት በመስገድ ተጠናቋል፡፡
ዘጋቢ፡- አድኖ ማርቆስ-ከደባርቅ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2RnNHCq
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m
