
“የሕዳሴ ግድብ 2ኛ ዙር የውኃ ሙሌት በስኬት መጠናቀቁ የኢትዮጵያዊያን ልዩ የድል ብስራት ቀን ነው” ጀኔራል ብርሃኑ ጁላ
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 12/2013 ዓ.ም (አሚኮ) “የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ 2ኛ ዙር የውኃ ሙሌት በስኬት መጠናቀቁ የኢትዮጵያዊያን ልዩ የድል ብስራት ቀን ነው” ሲሉ የኢፌዴሪ ጦር ኀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀኔራል ብርሃኑ ጁላ ተናገሩ።
ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ በሰጡት መግለጫ የግድቡ 2ኛ ዙር የውኃ ሙሌት በስኬት በመጠናቀቁ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።
“የግድቡ ውኃ ሙሌት አሁን ያለበት ደረጃ እንዲደርስ ኢትዮጵያዊያን በከፍተኛ ቁርጠኝነትና ትብብር ሠርተዋል”ያሉት ጀነራል ብርሃኑ፤ ግድቡ የሞላበት የዛሬው ዕለት “የኢትዮጵያዊያን ልዩ የድል ብስራት ቀን ነው” ብለዋል።
ኢትዮጵያ ማንንም አገር የመጉዳት ፍላጎትና ዓላማ እንደሌላት ገልጸው፤ የግድቡ የውኃ ሙሌትም ይህንን በተግባር ያረጋገጠ ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ አክለውም የሕወሓት አሸባሪ ቡድን መንግሥት ለትግራይ ሕዝብ የሰጠውን የጥሞና ጊዜ በመጠቀም ትንኮሳዎችን እያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።
አሸባሪ ቡድኑ ለትግራይ ሕዝብ ደንታ ቢስ መሆኑና ሕዝቡን ለከፋ ችግር ለመዳረግ ቆርጦ መነሳቱን አመላካች ስለመሆኑም ያረጋገጠ መሆኑን ገልጸዋል።
“የሐገር መከላከያ ሠራዊት ከመቼውም ጊዜ በላቀ መልኩ በጠንካራ ቁመና ላይ ይገኛል” ብለዋል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ።
በመሆኑም “አሸባሪ ቡድኑ ትንኮሳዎችን የሚቀጥል ከሆነ ሠራዊቱ በሚሰጠው ትዕዛዝ አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ ነው” ሲሉ አረጋግጠዋል።
የትግራይ ሕዝብም በተሰጠው የጥሞና ጊዜ በመጠቀም አሸባሪውን የሕወሓት ቡድን “ሊዋጋውና በቃህ ሊለው ይገባል” ብለዋል። ኢዜአ እንደዘገበው፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
 
             
  
		