
በጣና ሐይቅ በተሰወረችው ጀልባ ህይወታቸው ያለፈ የሰባት ሰዎች አስከሬን ተገኘ።
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 12/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ምሥራቅ ደንቢያ ወረዳ በጣና ሐይቅ 13 ሰዎችን አሳፍራ በጉዞ ላይ እንዳለች በተሰወረችው አነስተኛ ጀልባ ህይወታቸው ያለፈ የሰባት ሰዎች አስከሬን መገኘቱን ፖሊስ አስታወቀ።
የወረዳው ፖሊስ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ምክትል ኮማንደር ቸርነት አስማረ እንደገለጹት አስከሬኑ የተገኘው በሐይቁ ላይ ላለፉት ሁለት ቀናት በጀልባና በዋናተኞች በተካሄደ አድካሚ ፍለጋ ነው፡፡
አስከሬኑ የጣና ሀይቅ በሚያዋስናቸው በጎርጎራና አዲስጌ ድንጌ በተባለ የገጠር ቀበሌ መካከል በሐይቁ ላይ በማዕበል ተገፍተው ዛሬ ንጋት ላይ ተንሳፈው መገኘቱን አስረድተዋል፡፡
የቀሪውን የስድስት ሰዎች አስከሬን ለማግኘት ፍለጋው ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁመው የጀልባዋን መስመጥ የሚያጣራ ግብረ ኀይል ተቋቁሞ ምርመራ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡
ጀልባዋ ሐምሌ 9/2013 ዓም ሌሊት ድንች የጫኑ 13 ሰዎችን አሳፍራ በወረዳው አዲሰጌ ድንጌ ተብሎ ከሚጠራ ቀበሌ አባን ላይ ጎጥ መነሻዋን በማድረግ ወደ ጎርጎራ ወደብ በጉዞ ላይ እንዳለች መሰወሯ ይታወሳል።
የጀልባዋ መነሻና መድረሻ የሐይቅ ላይ ጉዞ የ15 ኪሎ ሜትር ርቀት እንዳለውም ኢዜአ ትላንት መዘገቡ ይታወሳል።
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
