
ቤተ እስራኤላውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለመተከል እና አካባቢው ተፈናቃይ ወገኖች የምግብ እና አልባሳት ድጋፍ አደረጉ፡፡
ባሕር ዳር: ሐምሌ 11/2013 ዓ.ም (አሚኮ) ቤተ እስራኤላዊያን እና በሀገሪቱ የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለመተከል እና አካባቢው ተፈናቃዮች አጋርነታቸውን አሳይተዋል፡፡
የድጋፍ አሰባሳቢ ተወካይ አቶ አንዳርጋቸው ክንፈሚካኤል የተደረገው ድጋፍ የምግብ እና አልባሳት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የተደረገው ድጋፍ ከ66 ሺህ ዶላር በላይ እንደሆነ የተናገሩት አቶ አንዳርጋቸው ወደፊትም ድጋፉ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡

የአማራ ክልል አደጋ መከላከል፣ ምግብ ዋስትና ፕሮግራም እና ልዩ ድጋፍ የሚሹ አካባቢዎች ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘላለም ልጃለም ቤተ እስራኤላውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ካሁን ቀደም በቻግኒ መጠለያ ጣቢያ ተገኝተው ድጋፍ ማድረጋቸውን አስታውሰዋል፡፡ አሁን የተደረገው ድጋፍም ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በውጭ ሀገር ያሉ ኢትዮጵያውያን ተፈናቃይ ወገኖችን በተቻላቸው አቅም እየደገፉ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ አሁንም ይህንን መልካም ተግባር አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ዘጋቢ፡- አሻግሬ መንገሻ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ