
የሶማሌ ክልል አሸባሪው ህወሃትን እስከመጨረሻው ለማስወገድ የአማራ ክልላዊ መንግሥትና የፌደራል መንግሥት የሚያደርገውን እንቅስቃሴ እንደሚደግፍ አስታወቀ።
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 09/2013 ዓ.ም (አሚኮ) አሸባሪው ህወሃት አሁን ላይ የመላው ኢትዮጵያውያን ስጋት እየሆነ መምጣቱን ተከትሎ ሁሉም ህብረተሰብ በአንድነት የሚቆምበት ጊዜ ላይ ስለመድረሳችን ማሳያ መሆኑን በመገንዘብ የሶማሌ ክልል መንግስት ይህንን ቡድን እስከመጨረሻው ለማስወገድ የሚደረገው ጥረት አካል በመሆን የአማራ ክልላዊ መንግስትና የፌደራል መንግስት የሚያደርገውን እንቅስቃሴ የሚደግፍ ይሆናል ብሏል።
የሶማሌ ክልላዊ መንግሥት በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሰጠው የአቋም መግለጫ ሙሉ ይዘት እንደሚከተለው ቀርቧል፡-
የሶማሌ ክልል ሕዝብና መንግስት ኢትዮጵያን በመበልፀግ ውስጥ ትልቅ አስተዋፅኦ ሲያበረክት የቆየ ህዝብ ነው። የሀገርና የህዝብ ሉአላዊነትና ነፃነትን ለማስከበር በሚከፈለው መስዋዕትነት ላይ ወደኋላ ብሎ አያውቅም።
በውጪ ወረራና በታሪክ አጋጣሚ የባንዳነትን ተግባር ሲፈጽሙ በነበሩት ኃይሎች ላይ በየታሪክ ምዕራፉ እራሱን ሰጥቶ ኢትዮጵያን የገጠሟትን ችግሮች ለማክሸፍ መስዋዕትነትን ከፍሏል።
ዛሬም እንደ ትላንንቱ የሶማሌ ክልላዊ መንግስት የክልሉን ህዝብ በማቀናጀት በወንድሞቻችን አብሮነት በኢትዮጵያ ላይ የሚሰነዘረውን የውስጥና የውጪ ትንኮሳ ለማክሸፍ ዝግጁ መሆኑን ይገልፃል።
የሶማሌ ክልላዊ መንግስት የፌደራል መንግስቱ የወሰደውን የተናጠል ተኩስ የማቆም እርምጃ ለሕዝብ ጥሩ የጥሞና ጊዜ የፈጠረ መሆኑን አምኖ ሲደግፍ ቆይቷል።
ይሁን እንጂ ከአፈጣጠሩ የተጣመመው ደም መጣጩ የሸማግሌዎችና የቤተሰብ ስብስብ ጁንታ ቡድን ለሕዝብ ጥቅም ተብሎ ለተደረገው ጥሪ ቦታ እንደሌለዉ በግልፅ አሳይቷል።
ለእድገታችንና የብልፅግና ጉዞ እንቅፋት በመሆን እንድንሸማቀቅ አድርጎናል። በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሀገርና ህዝብ በቀዳሚነት እየተጎዱ ነው።
አሸባሪው ሕወሃት እታገልላቸዋለሁ ብሎ የሚናገረውና በስማቸው እየኖረ ያለውን የትግራዋይ ሕዝብን ጨምሮ አስቦላቸው ወይም ተቆርቁሮላቸው አያውቅም።
ይህ ቡድን ትናንት የሐውዜን ህዝብ በሚገበያይበት ቦታ ላይ ቦምብ በማዝነብ የጅምላ ጭፍጨፋ ሲፈፅም ለፕሮፖጋንዳ ግብአትነት እንጂ ለሉአላዊነት ትግል አልዳልነበረ በግልፅ ያሳየ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬም ቢሆን በተባበሩት መንግስታት የወጣውን የሕፃናት መብት ድንጋጌ በመጣስ ጨቅላ ሕፃናትን ለጦርነት ከፊት አሰልፎ በመማገድ ላይ ይገኛል። አዛውንቶችን፣ እናቶችን እና የሐይማኖት አባቶችን እንደ ጋሻ ከፊት በማሰለፍ በእልቂታቸው የጀግንነት አክሊል ለመድፋት ይሞክራል።
አሁንም ቢሆን አሸባሪው ሕወሃት የፌደራል መንግስት ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን ካሳየው ፍላጎት በተቃራኒ በመሔድ ላይ ይገኛል።
በፌደራል መንግስት የታወጀው የተናጠል የተኩስ አቁም ስምምነት አርሶ አደሩ በክረምት ወቅት ተረጋግቶ እንዲያርስ፤ ለዜጎች እርዳታ እንዲደርስና ግጭት እንዳይባባስ ቢሆንም ጁንታው የተፈጠረበትን የጥፋት ስሜትና እጅ መቆጣጠር አልቻለም።
ስለሆነም የሶማሌ ክልል መንግሰት ህግን ለማስከበር ተከትሎ የፌዴራል መንግሰት መከላከያ ሰራዊቱን ለመደገፍ የተደረገውን ጥሪ በአጽንኦት ተቀብሎ ኃላፊነቱን እንደሚወጣ ያረጋግጣል።
ዛሬም ቢሆን ክልላዊ መንግስትና ሕዝብ የሀገር ሉዓላዊነት ጋሻ ከሆነው የመከላከያ ሠራዊታችን ጎን በመሆን ማናቸውንም መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ ነው። መንግስትም የህዝብ ተሳትፎን በማቀናጀት ሁለንተናዊ ስኬት ለማስመዝገብ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል።
የዚህ ቡድን ዓላማ በግልፅ ኢትዮጵያን መበታተን እና የቡድኑን የግል ፍላጎት ማሟላት ነው።
ቡድኑ ኢትዮጵያን የሚመራት አካል ከራሱ የወጣ አልያም እንዳሻው የሚዘውረው አካል መሆን አለበት የሚል አላማን ይዞ የሚንቀሳቀስ ቡድን ሲሆን ለዚህም ማዕከላዊ መንግስት ላይ ጥቃት በማድረስ የቀጠናውን ሰላም ለማደፍረስ እየሰራ ይገኛል።
የተቀረው የአለም ማህበረሰብ በትግራይ ክልል የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየተካሄደ ነው ብለው ትኩረት የሰጡትን ያህል አሁን ላይ ጁንታው ህፃናትን በአደንዛዥ እፅ በማደንዘዝ ለጦርነት ሲያሰልፍ እና ከላይ ለተገለጸው እኩይ አላማ መጠቀሚያ ሲያደርጋቸው ዝም ማለታቸው የሚያሳዝን ሆኖ አግኝተነዋል።
ቡድኑ አሁን ላይ የመላዉ ኢትዮጵያውያን ስጋት እየሆነ መምጣቱን ተከትሎም ሁሉም ህብረተሰብ በአንድነት የሚቆምበት ጊዜ ላይ ስለመድረሳችን ማሳያ መሆኑን በመገንዘብ የሶማሌ ክልል መንግስት ይህንን ቡድን እስከመጨረሻው ለማስወገድ የሚደረገው ጥረት አካል በመሆን የአማራ ክልላዊ መንግስትና የፌደራል መንግስት የሚያደርገውን እንቅስቃሴ የሚደግፍ ይሆናል።
በተለይ ይህ ቡድን በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ከከፈተው ጦርነት ባሻገር በአጠቃላይ የሀገሪቷን ፀጥታ ለማደፍረስ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ በመገንዘብ ድጋፋችን ውጤታማ እንዲሆን እስከመጨረሻው ድጋፋችን እንደሚቀጥልም ለመግለፅ እንወዳለን።
ትናንት በችግር ውስጥ የመንግስትን ጥሪን በመስማት ሁለንተናዊ ድርሻችሁን የተወጣችሁና የአሸባሪዎች የጥፋት መርዝ እንዲደፋ ያደረጋችሁ የክልላችን የህብረተሰብ ክፍሎች ዛሬም እንደ ትናንቱ የጎላ ተሳትፎአችሁን እንድታበረክቱ የሶማሌ ክልላዊ መንግስት ጥሪውን ያቀርባል።
የሶማሌ ክልላዊ መንግሥት
ሀምሌ 09 ቀን 2013 ዓ.ም
ጅግጅጋ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ