
‹‹ለሕልውና ዘመቻ ከወር ደመወዝ በተጨማሪ ደም እንሰጣለን›› የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ሠራተኞች
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 08/2013 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን (አሚኮ) ሠራተኞች ለሕልውና ዘመቻ በሙያቸው ከሚያደርጉት አበርክቶና የወር ደመወዝ ድጋፍ ባለፈ ደም እየለገሱ ነው፡፡
ደም ከለገሱ ሠራተኞች መካከል ጋዜጠኛ ይታገስ መንገሻ እንደተናገረው በተለያዩ ምክንያቶች ደም ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች በማሰብ በኮርፖሬሽኑ በየሦስት ወር ደም ይለግሳል፡፡
በአሁኑ ወቅት ደግሞ አሸባሪው ትህነግ የቃጣውን ትንኮሳ ለመመከት ህይወታቸውን እየሰጡ ለሚገኙ የሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ ለአማራ ልዩ ኀይልና ሚሊሻ ደም መለገሱን አስረድቷል፡፡
ደም መገለስ የሚችሉ የኅብረተሰብ ክፍሎችም አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡
በቀጣይም የወር ደምወዙን ለህልውና ዘመቻ ድጋፍ እንደሚያደርግም ተናግሯል፡፡
ሌላው የቀረጻና ቅንብር ምክትል ዳይሬክተር ሠራወርቅ ካሴ ካሁን ቀደም ደም የመለገስ ልምድ እንዳለው ገልጿል፡፡ በአሁኑ ወቅት ደም መለገስ ልዩ ትርጉም አለው፤ ምክንያቱም የህልውና ጉዳይ ነው ብሏል፡፡ ከደም ልገሳና ከሙያዊ አበርክቶው ባለፈ የወር ደመወዝ ድጋፍ እንደሚያደርግም ነው የተናገረው፡፡
ጋዜጠኛ መስከረም ተስፋዬ ደም ከለገሱ የኮርፖሬሽኑ ሠራተኞች አንዷ ናት፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ደም እንደለገሰች የገለጸችው መስከረም ይህንንም አጠናክራ እንደምትቀጥል ተናግራለች፡፡ ለህልውና ዘመቻው የወር ደምወዟን ድጋፍ እንደምታደርግም ገልጻለች፡፡
የኮርፖሬሽኑ ሠራተኞች ከሚያደርጉት ድጋፍ ባለፈ ግንባር ድረስ በመሄድ በሙያቸው ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዘጋቢ ፡- አዳሙ ሽባባው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ