
የውጪ ኢንቨስትመንትን 20 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ተናገሩ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሰኔ 28/ 2013 ዓ.ም (አሚኮ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) እንዳሉት የውጪ ኢንቨስትመንትን 20 በመቶ ማሳደግ ተችሏል፡፡ 2 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር በዓይነትና በመጠን ወደ ብሔራዊ ባንክ ገብቷል፡፡ ይህን ያክል የኢንቨስትመንት እድገት ማሳየት የቻሉት በአፍሪካ ጥቂት ሀገራት ብቻ መሆናቸውን አመላክተዋል፡፡
በሚቀጥለው ዓመት ኢንቨስትመንቱ የበለጠ ሊያድግ እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡ ይህን ለማሳካት ባለሃብቶችን በአግባቡ ማስተናገድ ያስፈልጋል ነው ያሉት፡፡
በኢንቨስትመንትና በቁጠባ መካከል ያለው ልዩነት እየጠበበ መምጣቱን የተናገሩት ጠቅላይ ሚንስትሩ ከ 2 ዓመታት በፊት በኢንቨስትመንትና በቁጠባ መካከል ያለው ልዩነት 14 ነጥብ 5 እንደነበረ አስታውሰዋል፡፡ ይህ ልዩነት ዘንድሮ በመሻሻል ወደ 9 ነጥብ 8 በመቶ መድረሱን አስረድተዋል፡፡ አሁን ያለው ቁጠባ ቢያድግ ተጨማሪ የውስጥ ኢንቨስትመንትን መፍጠር ይቻላል ብለዋል፡፡
በሀገሪቱ የህዳሴ ግድቡን ጨምሮ በርካታ የተለያዩ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ በመሆኑና የሲሚንቶ ፋብሪካዎች ምርታቸውን ስለቀነሱ የሲሚንቶ እጥረት መከሰቱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡ ለዚህም መንግሥት በተለያዩ አማራጭ መፍትሔዎችን ላይ እየሠራ ነው ብለዋል፡፡ ሲሚንቶ በሠፊው የሚያመርቱ ኩባንያዎችም መምጣታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል፡፡ ከሲሚንቶ ጋር የተያያዘው ችግር ቢያንስ ከአንድ ዓመት በኋላ እንደሚፈታ ነው የገለጹት፡፡
ዘጋቢ፡- ቡሩክ ተሾመ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ