
የአካባቢያቸዉን ሰላም ለማስጠበቅ ሲሉ ሕይወታቸውን ላጡ የፓሊስ፣ የሚሊሻ እና የልዩ ኀይል ቤተሰቦች የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን የዋግ ልማት ማኀበር አስታወቀ።
ባሕር ዳር፡ ሰኔ 27/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በአበርገሌ እና በፃግብጂ ወረዳ አከባቢያቸውን ለመጠበቅ ሲሉ ሕይወታቸውን ላጡ ቤተሰቦች በሰሜን አሜሪካ፣ በአውሮፓ እና አውስትራሊያ የሚኖሩ የዋግ ተወላጆች እና የልማት ማኀበሩ ደጋፊዎች የተሰበሰበ ከ436 ሺህ ብር በላይ በማኀበሩ አስተባባሪነት ለተጎጂዎች መሰጠቱን የማኀበሩ ምክትል ዳይሬክተር እና የገቢ ማስገኛ ተቋማት አስተባባሪ ሙላው ደምሴ ተናግረዋል።
የጤና፣የትምህርት፣የተፈጥሮ ሀብት፣የባህል፣የቋንቋና የታሪክ ልማት ፕሮግራሞችን ቀርፆ ልማት ማኀበሩ እየሠራ እንደሚገኝ የገለጹት አቶ ሙላው የኢኮኖሚ ችግር ላለባቸው የማኅበረሰብ ክፍሎች ድጋፉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።
የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የአደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ አቶ መልካሙ ደስታ በዋልማ አስተባባሪነት ለተደረገው ድጋፍ በማመስገን ለተጎዱ የማኅበረሰብ ክፍሎች በመንግሥት ከሚደረገው ጊዚያዊ ድጋፍ በተጨማሪ በዘለቄታ ለማቋቋም ሁሉም ማኀበረሰብ ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አስተላልፈዋል።
ድጋፍ የተደረገላቸው የተጎጂ ቤተሰቦችም ለተደረገላቸዉ ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ፀጋየ አይናለም-ከሰቆጣ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ