ከ16ሺህ በላይ የመተከል ዞን ተፈናቃዮችን ወደ ቀያቸው የመመለስ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የግብረ ኃይሉ ቴክኒክ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡

167
ከ16ሺህ በላይ የመተከል ዞን ተፈናቃዮችን ወደ ቀያቸው የመመለስ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የግብረ ኃይሉ ቴክኒክ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሰኔ 16/2013 ዓ.ም (አሚኮ) ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ከስድስት ወረዳዎች የተፈናቀሉ ወገኖች ላለፉት ወራት በቻግኒ ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው ራንች ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያ መቆየታቸው ይታወቃል፡፡
ከቤኒሻንጉል ጉሙዝና ከአማራ ክልል የተውጣጣው የጋራ ግብረ ኀይልና ኮማንድ ፖስት በሠራው ሥራ ሰኔ 11/2013 ዓ.ም በመጀመሪያው ዙር የመመለስ ሥራ ተፈናቃይ ወገኖችን ወደ ማንዱራ እና ዳንጉር ወረዳ መመለሳቸውን አሚኮ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ዛሬ ደግሞ ወደ ቡለን፣ወምበራና ድባጤ ወረዳ ተፈናቃዮችን ወደ ቀያቸው የመመለስ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ የግብረ ኀይሉ የቴክኒክ ኮሚቴ አባል አቶ በትግሉ ተስፋሁን ተናግረዋል፡፡
ዜጎች ወደ ቀያቸው ተመልሰው መደበኛ ሕይወት እንዲመሩ ከኮማንድ ፖስቱ እና ከቴክኒክ ኮሚቴው ሰፊ ሥራ ሲሠራ መቆየቱንም አቶ በትግሉ አስታውሰዋል፡፡
ወደ ቀያቸው ለሚመለሱ ዜጎች መንግሥት መሰረተ ልማቶችን በማሟላት መደበኛ ሕይወት እንዲመሩ እየሠራ መሆኑንም አቶ በትግሉ ገልጸዋል፡፡ በሂደትም የሰላሙ ሁኔታ አስተማማኝ ሲሆን ነዋሪዎች ወደ እርሻና ሌሎች ሥራዎች ይመለሳሉ ብለዋል፡፡
ዛሬ ወደ ቀያቸው ለሚመለሱ ነዋሪዎች የአካባቢው ኀበረተሰብ አቀባበል ሊያደርግላቸው ዝግጅት እያደረገ እንደኾነም ነው የነገሩን፡፡ ይህም በሕዝብ ለሕዝብ ያለውን ጠንካራ ትስስር ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ወደ ቀያቸው ለሚመለሱ ተፈናቃዮች ጥበቃ ይደረግላቸዋል ብለዋል፡፡
ከዚህ በፊት ወደ ቀያቸው የተመለሱት የማንዱራና የዳንጉር ወረዳ ነዋሪዎችም የተረጋጋ ሕይወት እየመሩ መሆናቸውን እንዳረጋገጡም አቶ በትግሉ ገልጸዋል፡፡ እስከ አሁን የተመለሱትን ጨምሮ ከ50ሺህ በላይ የተፈናቀሉ ወገኖችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ ግብረ ኀይሉ እየሠራ እንደኾነ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ዘጋቢ፡- አዳሙ ሽባባው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous articleቦርዱ ለክልሎችንና ከተማ አስተዳደሮች የምርጫ ቁሳቁስና ሰነዶች ከምርጫ ክልል ወደ አዲስአበባ በማጓጓዝ ሂደት ትብብር እንዲያደርጉለት ጠየቀ።
Next articleበደቡብ ክልል ድምጽ የተሰጠባቸው 98 በመቶ የምርጫ ቁሳቁስ ወደ ምርጫ ክልል ገብቷል፡፡