
“በኦሮሚያ ክልል ስሜን ሽዋ ዞን በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች 96 ነጥብ 8 በመቶ መራጮች ድምጽ ሰጥተዋል” የዞኑ ምርጫ ቦርድ ማስተባበሪያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት
ባሕር ዳር፡ ሰኔ 15/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በኦሮሚያ ክልል ስሜን ሽዋ ዞን የምርጫ ቦርድ ማስተባበሪያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት አስተባባሪ አቶ መልካሙ ተክሌ በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች ለመምረጥ ግማሽ ሚሊዮን ሕዝብ በመራጭነት ተመዝግቦ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ለመምረጥ ከተመዘገበው ውስጥም 96 ነጥብ 8 በመቶ የሚሆነዉ መራጭ ድምጽ መስጠቱን ጠቁመዋል፡፡
አቶ መልካሙ እንደገለፁት በዞኑ ብልፅግና፣ ኢዜማ፣ አብን እና እናት ፓርቲዎች ተወዳድረዋል። እስካሁንም ከፓርቲም ሆነ ከመራጩ ሕዝብ ምንም አይነት ቅሬታ አልቀረበም ብለዋል።
“ምርጫው በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች ያለምንም የጸጥታ ችግር ተጠናቋል፡፡ ውጤታማም ነበር፡፡ ሕዝቡም በነጻነት እና በፍትሐዊነት ድምጹን ሰጥቷል” ነው ያሉት፡፡
በአሁኑ ስዓትም በብዙ የምርጫ ጣቢያዎች ቆጠራው ተጠናቆ ጊዜያዊ የመራጮች የድምጽ ውጤት መገለጹንም ጠቁመዋል። አሚኮም የሕዝብ ድምጽ ጊዜያዊ ውጤት መገለጹን ተመልክቷል።
ዘጋቢ፡- በለጠ ታረቀኝ -ከፍቸ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ