የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር ሁለተኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን እያካሄደ ነው።

219

የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር ሁለተኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን እያካሄደ ነው።
ባሕር ዳር፡ ግንቦት 22/2013 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር በአዲስ አበባ በካፒታል ሆቴል
እያደረገ በሚገኘው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ሊጉ የስያሜ እና የስርጭት መብቱን በመሸጡ በዚህ ዓመት የተገኘው ገቢ ይፋ የተደረገ
ሲሆን በምን መልኩ እንደተከፋፈለም ገለፃ ተደርጓል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ጂራ በጉባኤው ላይ እንዳሉት አክሲዮኑ በተቋቋመ አጭር ጊዜ ውስጥ
ውጤታማ ሥራዎችን ሠርቷል፤ ለአብነትም በተሻለ ሁኔታ በመምራቱ ውድድሩ በጊዜ ተጠናቋል፤ በራሱ ገንዘብ ኖሮት ለሁሉም
ክለቦች በየደረጃቸው ገንዘብ እንዲያገኙ አድርጓል፤ ይህ ተሞክሮም በኢትዮጵያ እግር ኳስ የመጀመሪያ ነው።
ፕሪሚየር ሊጉ የቀጥታ ስርጭት ሽፋን ማግኘት ጋር ተያይዞም የተጫዋቾች አቅምና ብቃት በተጨባጭ መሻሻሉን ፕሬዝዳንቱ
አንስተዋል። የፕሪሚየር ሊጉ በሱፐር ስፖርት እና በዲኤስ ቲቪ መተላለፍ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘትም ረገድ ሚና እንደነበረው
ተናግረዋል፡፡
ስታዲየሞች በተለይ በክረምት ምቹ አለመኾናቸውን የጠቀሱት ፕሬዝዳንቱ በቀጣይ እግር ኳሱ በዓለም አደባባይ ስለሚታይ
የሚመጥኑ ስታዲየሞች እንደሚያስፈልጉ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ እና
የመጫወቻ ሜዳዎች ጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ እዲሆኑ መሠራት እንዳለበትም አንስተዋል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ተጨባጭ ለውጥ እና እድገት እንዲያመጣ ታዳጊዎች ላይ መሠራት አለበት ብለዋል፡፡ በቀጣይ ዓመትም
ሁሉም የፕሪሚየር ሊጉ ክለቦች ከ17 ዓመት በታች ቡድን መያዝ ግዴታቸው እንደሆነ ፕሬዝዳንቱ አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር ቦርድ ስብሳቢ መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞ ሊጉ በዲኤስ ቲቪ እንዲተላለፍ ስምምነት
ለመድረስ የነበረው ሂደት ረዥም ርቀት የፈጀና ውስብሰብ እንደነበር አንስተዋል፡፡ በዓመቱ ከዲኤስ ቲቪ ጋር ስምምነት የተደረገው
60 ጨዋታዎችን ለማስተላለፍ እንደነበር እና በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ጨዋታዎች በተመረጡ ስታዲየሞች መካሄዳቸው
በዓመቱ 155 ጨዋታዎች እዲተላለፉ አድርጓል ብለዋል።
የኢትዮጵያን መልካም ገፅታ፣ ባሕል እና እሴት ለዓለም በማስተዋወቅና አጠቃላይ ቱሪዝም ላይ የተሠራው ሥራም ትልቅ እንደነበር
ነው ሰብሳቢው ያነሱት። ተጫዋቾችን ጨምሮ ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንደ ጀማሪ ሳይሆን ሙያቸውን አክብረው በመሥራታቸው
ከ90 በመቶ በላይ ስኬታማ ውድድር መካሄዱንም ገልጸዋል።
አክሲዮን ማኅበሩ ለሊጉ ተሳታፊዎች ያከፋፈለውን የገንዘብ መጠንም አስታውቋል። መቶ አለቃ ፈቃደ የክፍፍሉን አካሄድ ከሌሎች
ሀገራት በተለይም የእንግሊዝ ልምድን መውሰዳቸውን ጠቁመው ከገቢው 60 በመቶ ሁሉም ክለቦች እኩል እንዲከፋፈሉ፣ 25
በመቶ በደረጃቸው እንዲሁም 15 በመቶ ለሊግ ካምፓኒው የሥራ ማስፈፀሚያ እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል።
ዘጋው፡- ባዘዘው መኮንን- ከአዲስ አበባ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2RnNHCq
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m

Previous articleወጣቶች ከመንግሥት ጎን በመቆም የውጭ ኃይሎችን ጣልቃ ገብነት እና የውስጥ ተላላኪዎችን ሴራ እንዲያከሽፉ ተጠየቁ፡፡
Next articleየአማራ ሚደያ ኮርፖሬሽን የሚዲያ ተደራሽነትን ለማሳደግ እየሠራ ነው።