
“ረመዳን ሕዝበ ሙስሊሙ፣ በመተዛዘን፣ በመደጋገፍና በመረዳዳት በፆምና በሶላት የሚያሳልፍበት የተቀደሰ ልዩ ወር ነው” የአማራ ክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት የእርዳታና ልማት ዘርፍ ኀላፊ ሐጂ አሕመድ አሊ።
ባሕር ዳር፡ ግንቦት 03/2013 ዓ.ም (አሚኮ) የረመዳን ወር ጾም በእስልምና ሃይማኖት የተከበረና የተቀደሰ እንዲሁም ከሃይማኖቱ አምስቱ መሠረቶች ውስጥ አንዱ ነው። የረመዳን ፆም ምን እንደሆነ፣ በወሩ ምን አይነት ተግባራት እንደሚፈጸሙ የአማራ ክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት የእርዳታና ልማት ዘርፍ ኀላፊ ሐጂ አሕመድ አሊ ጠይቀናል።
ሐጅ አሕመድ “ረመዳን በጎ ተግባራት የሚከናወኑበት፣ ያለው ለሌለው የሚለግስበት ሁሉም ሰው በሠራው ልክ ከአላህ በእጥፍ የሚያገኝበት ክቡር የፆም ወር ነው” ብለዋል።
በእስልምና የዘመን አቆጣጠር (ሂጅራ) 12 ወራቶች አሉ፤ ከእነዚህ ወራቶች ውስጥ ረመዳን በዘጠነኛው ወር ይፆማል፤ የረመዳን ወር ከሌሎች ወራት በተለየ በመደጋገፍና በመተዛዘን የሚያሳልፍበት ወር መሆኑን ሐጅ አሕመድ አስረድተዋል። “በረመዳን የጀሀነም ደጅ የሚዘጋበትና የጀነት በር የሚከፈትበት እንዲሁም ሸይጣን የሚታሰርበት ወር ነው” ብለዋል።
“ረመዳን ሕዝበ ሙስሊሙ፣ በመተዛዘን፣ በመረዳዳት በፆምና በሶላት ቁርዓን በመቅራት የሚያሳልፍበት የተቀደሰ ልዩ ወር ነው” ብለዋል ሐጅ አሕመድ በገለጻቸው።
በረመዳን ወር ማገባደጃ አካባቢ ደግሞ በመረዳዳትና በመደጋገፍ የተሠራው ሥራ ሁሉ በፈጣሪ ዘንድ ተቀባይ እንዲሆኑ፣ የተጓደለው ሁሉ ሙሉ እንዲሆን የዘካተልፊጥር ሥርዓት እንደሚከናወን አስረድተዋል።
በፆሙ መጨረሻ ላይ ኢድ አልፈጥር ከመግባቱ በፊት አቅም ያለው ሁሉ ካለው አውጣጥቶ ለአቅመ ደካሞች ዘካተልፊጥር እንደሚደረግላቸው ተናግረዋል።
የረመዳን የፆም ወር በእስልምና ሃይማኖት ልዩ ትኩረት እንደሚሰጠው የጠቆሙት ኀላፊው “ተራዊ ሶላት” በረመዳን ወር ብቻ የሚተገበር መሆኑ ደግሞ ወሩን ከሌሎች ወራቶች ልዩ ያደርገዋል ብለዋል።
ዘጋቢ:- ቡሩክ ተሾመ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ