ማኅበረሰቡ በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን በሌሎች ወቅቶችም የመረዳዳት ባህሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል የአማራ ክልል ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ጠየቀ።

225
ማኅበረሰቡ በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን በሌሎች ወቅቶችም የመረዳዳት ባህሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል የአማራ ክልል ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ጠየቀ።
ባሕር ዳር፡ ሚያዝያ 21/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በባሕር ዳር ከተማ ለሚኖሩ 101 አረጋውያን የትንሣኤና የረመዳን በዓላትን ምክንያት በማድረግ ድጋፍ ተደርጓል፡፡
የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ መምሪያ ከክልሉ ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ እና ከከተማ አስተዳደሩ የአረጋውያን ማኅበር ጋር በመተባበር በባሕር ዳር ከተማ ለሚኖሩ ለ101 አረጋውያን ከ40 ሺህ ብር በላይ ድጋፍ አድርገዋል።
አቶ ማንደፍሮ አስረስ እና ወይዘሮ ቀኑ አበዜ የተባሉ አረጋውያን ከዚህ በፊት በዓልን ተቸግረው ይውሉ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ በዓልን ተደስተው እንዲውሉ ለተደረገላቸው ድጋፍም አመስግነዋል፡፡ ድጋፉ በሌሎች አካባቢዎችም ለሚኖሩ አረጋውያን ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። ሁሉም በአቅሙ አረጋውያንን እንዲደግፍም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ማኅበረሰቡ ለአረጋውያን ድጋፍ በማድረግ የቆየውን የመረዳዳት እና የመደጋገፍ ባህል ማጎልበት እንደሚገባው በባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ማኅበራዊና ሠራተኛ ጉዳይ መምሪያ ኀላፊ ጋሻው እንዳለው ተናግረዋል።
የአማራ ክልል ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ምክትል ቢሮ ኀላፊ ደረጀ አበጀ ማኅበረሰቡ በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን በመደበኛ ጊዜያትም የመረዳዳት ባህሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በክልሉ 1 ሺህ 550 አረጋውያን በቋሚነት በየወሩ የ300 ብር ድጋፍ እየተደረገላቸው እንደሚገኝ አቶ ደረጀ ገልጸዋል። በቀጣይም ሌሎች አረጋውያንን በቋሚነት ለመደገፍ የሚያግዙ ደረጃቸውን የጠበቁ ህንፃዎችን ለመገንባት እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
ለዚህም ሥራ በደቡብ ወሎ፣ ደቡብ ጎንደር፣ ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም ዞኖች ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ ተሰብስቧል፤ የህንፃዎቹ ዲዛይን ተሠርቷል፤ በሌሎች ዞኖች በሚገኙ 6 ወረዳዎችም ደረጃቸውን የጠበቁ ህንጻዎች በመገንባት ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል።
ዘጋቢ፡- ዳግማዊ ተሠራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous articleበበዓል ወቅት በሚጣል ቆሻሻ ለበሽታ ከመጋለጥ ሁሉም ዜጋ አካባቢውን በአግባቡ በማጽዳት ኀላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ የዳንግላ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡
Next article“የሐዲስ ኪዳኗ ሐሙስ”