በክልሉ ባጋጠመው የጸጥታ ችግር ወጣቶች ሕዝቡን ከጥቃት መጠበቅ እንደሚገባቸው በአማራ ክልል የተለያዩ አደረጃጀቶች ገለጹ፡፡

292
በክልሉ ባጋጠመው የጸጥታ ችግር ወጣቶች ሕዝቡን ከጥቃት መጠበቅ እንደሚገባቸው በአማራ ክልል የተለያዩ አደረጃጀቶች ገለጹ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሚያዝያ 11/2013 ዓ.ም (አሚኮ) የክልሉን ሕዝብ በኢኮኖሚ፣ በሥነልቦና እና በፖለቲካ ተሳትፎው ለማዳከም የሚሹ አካላት በሚያስነሱት ግጭት የሰው ሕይወት እየተቀጠፈ፣ በሀብትና በንብረት ላይም ከፍተኛ ውድመት እየደረሰ ነው፡፡
ድርጊቱ ሕዝብ ተረጋግቶ መደበኛ ሕይወቱን እንዳይመራ፣ አርሶ አደሮችም እንዳያመርቱ ለማደናቀፍና ወደ አልተፈለገ ቅጣጫ ለመክተት የታሰበ መሆኑ የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡ ‘ኦነግ ሸኔ’ የሚል መጠሪያ የተሰጣቸው ታጣቂ ኀይሎች የፈጠሩት የተደራጀ ወረራ ለዚህ ሁነኛ ማሳያ ነው፡፡
ድርጊቱ ሕዝቡን ወዳልተገባ ስሜት በመክተት ሀገርን ለመበታተን የተሠራ መሆኑን የአማራ ወጣቶች ማኅበር አስገንዝቧል፡፡ የአማራ ወጣትና ሕዝብ ድርጊቱን ስለተገነዘበ በሰብዓዊ ፍጥረት ላይ ሊፈጸም የማይገባ ግፍ ሲፈጸም በትዕግስት መመልከቱን የማኅበሩ ጸሐፊ ከፍያለው ማለፉ ተናግሯል፡፡
ተግባሩ የሚያስመሰግን መሆኑን በማንሳት ትዕግሥት እንደ የዋሕነት መቆጠር የለበትም ብሏል፡፡ በክልሉ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመከላከል ማኅበሩ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም አስታውቀዋል፡፡ ወጣቱ አሁንም ነገሮችን በሰከነ መንገድ ማየት እንዳለበትም ተናግሯል፡፡
“የክልሉ ወጣት በተደራጀ አግባብ የአማራ ሕዝብን ከጥቃት መከላከል አለበት” ያለው ጸሐፊው ወቅቱ አንድነትን የሚጠይቅ መሆኑን ገልጿል፡፡ ለዚህም ወጣቱ መደራጀትና አካባቢን በንቃት መጠበቅ እንደሚገባው አንስቷል፡፡
ለችግሮች የተጠና ምላሽ መስጠት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ከወጣቶች ጋር ውይይት እየተደረገ መሆኑንም አመላክቷል፡፡ የክልሉ መንግሥትና ወጣቶች በአንድነት እንዲሠሩ ማኅበሩ በትኩረት እየሠራ መሆኑንም ጠቅሷል፡፡
መንግሥት በጥቃት አድራሾች ላይ የማያዳግም ርምጃ በመውሰድ ሕግና ሥርዓትን ማስከበር አለበት፤ የጸጥታ መዋቅሩና የደኀንነት መረቡ ተቀናጅተው በመሥራት የዜጎችን ሞትና መፈናቀል እንዲሁም የንብረት ውድመት ማስቆም እንዳለባቸውም አሳስቧል፡፡
የአማራ ሴቶች ማኅበር ዋና ጸሐፊ ትጥቅነሽ አለሙ በዚህ ወቅት የአማራ ሕዝብ ያለውን ጠንካራ ሥነልቦና፣ የተረጋጋ ማንነትና ችግርን መክቶ የማለፍ ብቃቱን መጠቀም እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ለዚህም ውስጣዊ አንድነትን በማጠናከር ለችግር የተጋለጡ ወገኖችን መደገፍና ክልሉን ማረጋጋት ይገባል ብለዋል፡፡ በጉልበት፣ በሀብት፣ በዕውቀትና በሌላም በሚቻለው አቅም መተጋገዝ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡
ወጣቶችም ከስሜት ቀስቃሽና ተስፋ አስቆራጭ መረጃዎች ራስን በማራቅ የክልሉን ሠላም ማስጠበቅ እንደሚገባቸውም አንስተዋል፡፡ የገጠመውን ችግር ለመመከት የሕዝቡ ጠንካራ ሥነልቦና ወሳኝ መሆኑንም ነው ያብራሩት፡፡
1 ሚሊዮን 700 ሺህ አባላት ያሉት ማኅበሩ እስከቀበሌ ድረስ ባለው መዋቅር ከመንግሥትና ከጸጥታ አካላት ጋር በመሆን ለክልሉ ሠላም መስፈን የድርሻውን እንደሚወጣ ተናግረዋል፡፡ አባላቱም የተጎዱ ወገኖች ድጋፍ እንዲያገኙና በዘላቂነት እንዲቋቋሙ የማስተባበር ሚና ይጫወታልም ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፡-ደጀኔ በቀለ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous articleበኩር ጋዜጣ ሚያዝያ 11/2013 ዓ.ም ዕትም
Next articleከሰርጎ ገቦች ጥቃት አካባቢያቸውን እየጠበቁ መሆኑን የምንጃር ሸንኮራ ወረዳ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡