
ግብጽ የግድቡ ሁለተኛ ዙር የውኃ ሙሌት የሚፈጥርባት ጫና እንደሌለ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ገለጹ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሚያዝያ 08/2013 ዓ.ም (አሚኮ) ታላቁ የኢትዮጵያ ግዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውኃ ሙሌት በግብጽ ላይ የሚፈጥረው ጫና እንደሌለ ካለም ያንን ለመቋቋመ የሚያስችል በቂ ውኃ እንዳላት የግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሚ ሽኩሪ ለሀገሪቷ ፓርላማ አባላት ገልጸዋል።
ሁለተኛው ዙር የግድቡ ውኃ ሙሌት በግብጽ ላይ የሚያመጣው ጉዳት እንደሌለ ካለም ለመከላከል መንግሥታቸው በቂ ዝግጅት ማድረጉን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ በአስዋን ግድብ በቂ ውኃ መያዛቸውን አብራርተዋል።
“የተደረጉ የቴክኒክ ጥናቶችን ተንተርሼ ነው” ገለጻውን የምሰጣችሁ ያሉት ሚኒስትሩ፤ በዘንድሮው የክረምት ወራት ከፍተኛ ጎርፍ ይጠበቃል፤ ስለሆነም ኢትዮጵያ ግድቧን ውኃ ብትሞላም የሚፈጠር ጫና የለም ከተፈጠረም ጎርፉ ግድባችንን መልሰን ለመሙላት ያግዘናል ብለዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግብጽ ላይ ጉዳት አያስከትልም፤ ነገር ግን ጉዳት የሚያመጣ ከሆነ በዚህ ረገድ እንደ ሀገር ያንን ለመቋቋም የሚያስችል በሁሉም መስክ አስፈላጊ ሀብት አለን ሲሉ ሚኒስትሩ መግለጻቸውን አህራም ኦንላይን ዘግቧል።
ኢትዮጵያ የግድቡ መገንባት በግብጽ ላይ የሚፈጥረው ጫና እንደሌለ በተደጋጋሚ ስትገልጽ ቆይታለች፤ የግድቡ ውኃ አሞላልም የታችኛውን የተፋሰሱ ሀገራት በማይጎዳ መልኩ እንደምታከናውን መግለጿ አይዘነጋም።
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ