
የትግራይ ሚዲያ ሃውስ ጋዜጠኛ ፍፁም ብርሃኔ እና የአይጋ ፎረም ዋና አዘጋጅና የኢትዮጵያ ተወካይ ጋዜጠኛ ታምራት የማነ በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሚያዝያ 08/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በልዩ ዘመቻዎች ኀይል 2ኛ ኮማንዶ ብርጌድ 3ኛ ኮማንዶ ሻለቃ በትግራይ ክልል ሕግ በማስከበር ዘመቻ አመርቂ ግዳጅ መፈፀማቸው ተገለጸ።
የ3ኛ ሻለቃ ዋና አዛዥ ሻለቃ ደረጄ ዴቢሳ እንደገለፁት፣ በትግራይ በተደረገው ሕግን በማስከበር ዘመቻ ጠለት የሚመካባቸውን ምሽጎች በሶሮቃ፣ በዳንሻ፣ በባካር፤ በመሶበር፤ በጨርጨርና በአይደፈር ተራሮች ላይ የተገነቡ ምሽጎችን በመስበር የጠላትን ስትራቴጂካዊ ቦታዎችን በመቆጣጠር ታሪክ የማይረሳው ገድል ፈጽመዋል፡፡
አሁንም ሻላቃው የመቀሌ ከተማ ሁለንተናዊ የፀጥታ ሁኔታዎችን ለማረጋገጥ ለ24 ሰዓት በቀንና በሌሊት የፖትሮሊንግ ስራዎችን በመስራት በከተማዋ ውስጥ በግለሰብ እጅ የሚገኙ ከቀላል እስከ ቡድን መሣሪያዎችን በማስፈታት ስርቆትና ዝርፊያ መቀነስ መቻሉን ዋና አዛዡ ተናግረዋል።
በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር አመራር መዋቅር ውስጥ በመሆን ከፀረ ሰላም ኀይሎች ጋር እየሰሩ የነበሩ ግለሰቦችን ጨምሮ የትግራይ ሚዲያ ሃውስ ጋዜጠኛ ፍፁም ብርሃኔ እና የአይጋ ፎረም ኢዲቶሪያል ዋና አዘጋጅና የኢትዮጵያ ተወካይ ጋዜጠኛ ታምራት የማነ በመቀሌ ከተማ በግለሰብ ቤት ስቱዲዮ ተከራይተው የውሸት ፕሮፓጋንዳ በቀጥታ ስርጭት እያስተላለፉ እያሉ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አስታውቋል።
በግለሰቦቹ ቤት በተደረገው ፍተሻም ለጁንታው ታጣቂ ቡድን ወደ በረሃ ለመላክ የተዘጋጁ በርካታ መድኃኒቶች፤ አልባሳትና የፕሮፓጋንዳ ማሰራጫ የኤሌክትሮኒክ እቃዎችና በርካታ ዶክመንቶች በቁጥጥር ስር መዋሉን አዛዡ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት በመቀሌ ከተማ በሰፈነው ሰላም ሕዝቡ የዕለት ተዕለት ተግባሩን በሰላማዊ መንገድ እየፈጸመ ከመገኘቱም በተጨማሪ የኮማንዶ ሻለቃው አባላት ከመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ለትግራይ ክልል የሚደረገውን ሁለንተናዊ እርዳታና ድጋፎችን የተጠናከረ እጀባ በማድረግ ለኅብረተሰቡ እያደረሱ እንደሚገኙ የሻለቃው ዋና አዛዥ አክለው ገልጸዋል። መረጃው የመከላከያ ሚኒስቴር ነው፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ