
በቀጣይ አስር ዓመታት የኢንዱስትሪዎችን የቅባት እህሎች የግብዓት እጥረት ለመቅረፍ እየተሠራ መሆኑን የአማራ ክልል ግብርና
ቢሮ አስታወቀ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሚያዝያ 02/2013 ዓ.ም (አሚኮ) የቅባት እህሎች አቅርቦትን በዘላቂነት በማሳደግ የኢንዱስትሪዎችን የግብዓት
ፍላጎት ለማሟላት ያለመ ሀገርአቀፍ የውይይት መድረክ በባሕር ዳር ከተማ ተካሂዷል።
እንደ አማራ ክልል ግብርና ቢሮ መረጃ ኢትዮጵያ የቅባት እህሎችን ለማልማት በቂ መሬትና የተፈጥሮ ሀብት ባለቤት ብትሆንም
እስካሁን አልተጠቀመችበትም። በአማራ ክልል የምግብ ዘይት የሚያመርቱ ፋብሪካዎች ቢቋቋሙም የቅባት እህል ጥሬ እቃን
የሚያስገቡት ከውጭ ሀገራት ነው። ይህ ደግሞ ሀገሪቱን ዋጋ እያስከፈላት ነው።
የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኀላፊ መለስ መኮንን (ዶክተር) በቀጣይ አስር ዓመታት በክልሉ ያለውን የቅባት እህል እጥረት
ለመቅረፍ እቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡
በኢፌዴሪ ግብርና ሚኒስቴር የግብርና ኤክስቴንሽን ዋና ዳይሬክተር ገርማሜ ገሩማ እንደገለጹት ኢትዮጵያ በዓመት 350 ሺህ ቶን
ኩንታል የቅባት እህል ወደ ውጭ በመላክ 400 ሚሊዮን ዶላር ታገኛለች። በአንጻሩ የምግብ ዘይትን ከውጭ ሀገር ለማስገባት
600 ሚሊዮን ዶላር ወጭ ታደርጋለች። ይህን በሀገር ውስጥ በማምረትና ወደ ውጭ በመላክ ትኩረት ተሠጥቶ ሊሠራ ይገባል
ብለዋል።
የውይይቱ ተሳታፊ የ“ደብሊው ኤ” የዘይት ፋብሪካ የፕሮጀክት አስተባበሪ ወንድወሰን መኮንን በቂ የቅባት እህል ምርት በሀገር
ውስጥ ባለመመረቱ ከውጭ ሀገር ለመግዛት መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡ የዘይት ፋብሪካው በዓመት 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ቶን
ኩንታል በላይ ምርት ቢፈልግም ማግኘት ባለመቻሉ በሚፈለገው መጠን እያመረተ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ እንደ ሀገር የቅባት
እህሎች የሚመረቱት በመኸር ወቅት በመሆኑ የሚፈልጉትን ምርት በአንድ ጊዜ ለመግዛት የፋይናንስ እጥረት እንዳጋጠማቸውም
አንስተዋል፡፡ ችግሩን ለመፍታት የእርሻ ቦታ በማዘጋጀት እያመረቱ መሆኑን ነግረውናል፡፡
ሌላኛው ተሳታፊ የኮከብ ቃና ዘይት ፋብሪካ የሰሜን ቀጣና የእርሻዎችና የፕሮጀክት አስተባባሪ መልሰው ዳኜ የዘይት ምርቱን
በመላ ሀገሪቱ ለማዳረስ ቢፈልጉም የግብዓት እጥረት በመኖሩ አለማሳካታቸውን ጠቅሰዋል፡፡
እንደ አስተባባሪው ማብራሪያ ችግሩን ለመቅረፍ ፋብሪካው ከመንግሥት 9 ሺህ ሄክታር መሬት ወስዶ እያመረተ ነው ብለዋል፡፡
በተጨማሪ በፋብሪካው የእርሻ አካባቢ ለሚገኙ አርሶ አደሮች ግብዓቶችን በማቅረብ ለፋብሪካው ግብዓት የሚሆን ምርት
እንዲያመርቱ እየተደረገ መሆኑን ነግረውናል፡፡
መንግሥት ያለባቸውን የፋይናንስ እጥረት እንዲፈታላቸውም ጠይቀዋል፡፡
የአማራ ክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጥላዬ ተክለወልድ (ዶክተር) በተለያዩ የምርምር ማዕከላት የተሻሻሉ
የቅባት እህል ዝርያዎችን ( አኩሪ አተር፣ ሠሊጥ እና ሱፍ) እያባዙ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በምርምር ማዕከላት ሰሊጥ በሄክታር አስር ኩንታል እንዲሁም በመስኖ 20 ኩንታል እየተመረተ ነው ብለዋል፡፡ ዶክተሩ እነዚህን
አዳዲስ የቅባት እህል ዝርያዎች ለአርሶ አደሮች በማስተዋወቅ ማባዛት ይገባል ብለዋል፡፡ እስካሁንም አኩሪ አተር በምዕራብ
ጎንደር አርማጭሆ ወረዳ፣ ሱፍ በአዴት ግብርና ምርምር ማዕከል የወጡ አዳዲስ ዝርያዎች መሆናቸውን ነግረውናል፡፡ የቅባት
እህሎችን በመስኖ በማልማት ውጤታማ ሥራ መሥራት ተገቢ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ትርንጎ ይፍሩ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m