
“እርስ በርስ ከተደጋገፍን በቱሪዝም ዘርፍ ተዓምር መሥራት ይቻለናል” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 14/2013 ዓ.ም (አብመድ) ወደ አማራ ክልል ርእስ መዲና ባሕር ዳር ጎራ ያሉ ሁሉ የከተማውን ከፊል ገፅታ
በምድር ላይ ሆኖ ማየት ቢያሻቸው ቤዛዊት ግንባር ቀደም ቦታ ነው፡፡ የባሕር ዳር ከተማ የውበቷ ድምቀት፤ የጌጧ ብርሃን የሆኑት
መቀነቷ ዓባይና ጣና አብሮነታቸውን አጠናቀው ዓባይ በጣና ላይ ሲነጉድ ለማስተዋል ቤዛዊት ልዩ ስፍራ ነው፡፡ ግን ቤዛዊት ተራራ
ብቻ አይደለም፡፡ ቤዛዊት ባሕር ዳርን ቤት ለእንቦሳ! ላሏት ታላላቅ እንግዶች እምቦሳ እሰሩ! ያለችበት አድባር፤ ነገሥታትና
መኳንንት ግብር ያበሉበት ደብር፤ ስዩመ መንግሥት እና የአማራ ሕዝብ አንዱ ታሪካዊ ስፍራ ነበረ – የቤዛዊት ቤተ መንግሥት፡፡
በወቅቱ የሃገሪቱ መሪ የነበሩት ንጉሠ ነገሥት ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ በአካባቢው ቤተ መንግሥት ይኖራቸው ዘንድ ይፈልጉ
ነበር፡፡ ፍላጎታቸውንም በወቅቱ የባሕር ዳር አውራጃ አስተዳዳሪ ለነበሩት ፊታውራሪ ኃብተ ማሪያም ወልደ ኪዳን ለቤተ መንግሥት
የሚሆን ቦታ በባሕር ዳር እንዲመርጡ ትዕዛዝ አስተላለፉ፡፡
ዋና አስተዳዳሪው ኃብተ ማሪያምም ፈልገውና አፈላልገው የቤዛዊት ኮረብታማ ቦታን የቤተ መንግሥት መቀመጫ ይሆን ዘንድ
ለንጉሡ ነገሯቸው፡፡ በወቅቱም የንጉሡ ሚኒስትሮች የተለየ ሃሳብ ቢያቀርቡም ቤዛዊት በንጉሠ ነገሥቱ በጎ ፈቃድ ለቤተ
መንግሥት መቀመጫነት ታጨች፡፡
ወቅቱ የካቲት 10 ቀን 1958 ዓ.ም የያኔው የፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ያሁኑ የፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ
ካቴደራል እና የቤዛዊት ቤተ መንግሥት ግንባታ በንጉሠ ነገሥቱ የመሰረት ድንጋይ ተቀመጠ፡፡
የቤዛዊት ቤተ መንግሥት ግንባታ ወዲያውኑ ተጀምሮ ከሁለት ዓመታት የግንባታ ቆይታ በኋላ በ1960 ዓ.ም የመሰረት ድንጋዩን
ባስቀመጡት ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ተመርቆ ሥራ ጀመረ፡፡ ንጉሠ ነገሥቱም በተለያዩ ጊዜያት የእረፍት ጊዜ እንዳሳለፉበትም
ይነገራል፡፡ ከንጉሡ የንግሥና ዘመን ማብቃት በኋላ ላለፉት 50 ዓመታት የቤዛዊት ቤተ መንግሥት ምዕራፍ እና ታሪክ በዝግ ያለፈ
ነበር፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 11ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የቤዛዊት ቤተ መንግሥት ወደ ባለአምስት ኮከብ ዘመናዊ ሆቴል ለመቀየር ሥራ መጀመሩን
ገልጸዋል፡፡ ከጣና እስከ ጎርጎራ ለምንሠራው የቱሪዝም መንደር የቤዛዊት ቤተ መንግሥት ልዩነት ይፈጥራል ያሉት ጠቅላይ
ሚኒስትሩ የቤዛዊትን ቤተ መንግሥት አዲስ ከሚሠራው የዓባይ ድልድይ ጋርም አስተሳስረውታል፡፡
“እርስ በርስ ከተደጋገፍን በቱሪዝም ዘርፍ ተዓምር መሥራት ይቻለናል” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከቱሪስት መስህብ
ከሚፈጠረው የሥራ ዕድል፣ ከሚገኘው ገንዘብ እና በውጭው ዓለም ዝናዋ ከሚናኘው ኢትዮጵያ ሌላ ዕድል አለው ብለዋል፡፡
ለባሕር ዳር ተፈጥሮ ከለገሳቻት ውበት ላይ ዓይናችን ገልጠን ትንሽ ነገር ብናለማ፣ የጣና ሐይቅ ገዳማትን ለረጅሙ ጉዟችን
ማረፊያ ብናደርጋቸው፣ ጎርጎራ ተዝቆ ከማያልቀው ውበቷ ላይ የጀመርነውን ብንጨርስ እና ታሪካዊቷን የጎንደር ከተማ ከውቢቷ
ባሕር ዳር ጋር ብናስተሳስራቸው ሀገራዊ አንድነት ለማጠንከር በቂ መዳረሻ ይሆኑናል ብለዋል፡፡
“በባሕር ዳር ብዙ የጋምቤላ፣ ብዙ የቤንሻንጉል እና ብዙ የኦሮሞ ቱሪስቶች ያስፈልጋሉ፤ ምክንያቱም ሀገር አለማዎቃችን ሀገር
እንድናፈርስ አድርጎናልና፤ ሀገር አለማዎቃችን ሞምባሳን እና ዱባይን እንድናውቅ አስገድዶናል” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ
የላላ ለመሰለው ሀገራዊ አንድነት ቱሪዝም ሌላ ገፀ በረከት እንዳለው ለምክር ቤት አባላቱ ገልፀዋል፡፡
መሰል ፕሮጀክቶችን ሰንሠራ የገንዘብ ድጋፍ ያስፈልጋልና ለመደገፍ እንድትዘጋጁ ሲሉም አባላቱን ጠይቀዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ታዘብ አራጋው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m