በደብረታቦር ከተማ የሚሠሩ መሠረተ ልማቶች መጓተት እና የጥራት መጓደል ሊስተካከል እንደሚገባ ነዋሪዎች ጠየቁ።

188

በደብረታቦር ከተማ የሚሠሩ መሠረተ ልማቶች መጓተት እና የጥራት መጓደል ሊስተካከል እንደሚገባ ነዋሪዎች ጠየቁ።
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 06/2013 ዓ.ም (አብመድ) የዓለም ባንክ የከተሞችን ዕድገት ያገናዘቡ መሰረተ ልማቶች እንዲሰሩ ድጋፍ
እያደረገ ይገኛል። የደብረታቦር ከተማም ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ የዓለም ባንክ በጀት ተጠቃሚ በመሆኗ የተለያዩ መሠረተ ልማቶች
እየተከናወኑ ይገኛል።
የደብረታቦር ከተማ ነዋሪዋ ጥሩ ፈረደ መሠረተ ልማቶች የሚሰሩባቸው አካባቢዎች አዳዲስ ሠፈሮች በመሆናቸው በክረምት
ወቅት መንቀሳቀስ እንደማይቻል ነግረውናል።
አሁን ላይ አካባቢው በዓለም ባንክ በጀት የጌጠኛ ድንጋይ ንጣፍ መሠራቱ ችግሩን እንደሚያቃልለው ተናግረዋል። ይሁን እንጅ
የመሠረተ ልማቶች መጓተት እና የጥራት መጓደል በመኖሩ በትኩረት ሊሠራ አንደሚገባው አንስተዋል።
መንግስቱ ታደሰ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪም የዓለም ባንክ ለደብረታቦር ከተማ አስተዳደር የተለያዩ መሰረተ ልማቶችን በመሥራትና
ለወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህ ዓመት ሥራው ቀድሞ ቢጀመርም መንገድ፣ መብራት፣ ስልክና ውኃ ተናበው ባለመሥራታቸው ምክንያት አንዱ ሲገነባ
ሌላው እያፈረሰ በመሆኑ ሥራው በሚፈለገው ፍጥነት እና ጥራት እንዳልሄደ አንስተዋል።
የሚገነቡ መሠረተ ልማቶች የከተማዋን የወደፊት ዕድገት የሚመጥኑ እንዲሆኑም ጠይቀዋል። የተጀመሩ መሠረተ ልማቶች
በወቅቱና በጥራት እንዲጠናቀቁ ሁሉም ኃላፊነቱን መወጣት እንዳለበት መክረዋል።
የደብረ ታቦር ከተማ አስተዳደር ከተማ ልማት ቤቶችና ኮንስትራክሽን አገልግሎት ጽሕፈት ቤት የኮንስትራክሽን ዘርፍ ምክትል ሥራ
አስኪያጅ ዮርዳኖስ ቀለምወርቅ በ2012 ዓ.ም በዓለም ባንክ በተመደበ 104 ሚሊዮን ብር እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ
የመሠረተ ልማቶች መሠራታቸውን ገልጸዋል።
በዚህ በጀት ዓመት ደግሞ 125 ሚሊዮን ብር ተመድቧል፤ የመንገድ ዳር መብራቶች፣ የአረንጓዴ ልማት ፕሮጀክት፣ የፍሳሽ ቆሻሻ
ማስወገጃ ታንከር እና የሕዝብ ሽንት ቤት ግንባታን ጨምሮ የ39 ፕሮጀክቶች ሥራ እየተከናወነ ይገኛል። ከተመደበው በጀት አሥር
በመቶው ለጠጠር መንገድ፣ ለጌጠኛ መንገድ ግንባታ እና ለተፋሰስ ጥገና ሥራ የሚውል ነው። እስከ አሁንም ከአጠቃላይ
ሥራው ከ50 በመቶ በላይ መከናወኑንና በዘርፉ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ምክትል ሥራ አስኪያጁ
ገልጸዋል።
ይሁን እንጅ የብረት እና የሲሚንቶ ዋጋ ግሽበት፣ ከቴክኒክና ሙያ ኢንተርፕራይዝ የተደራጁ ተቋራጮች ልምድ ማነስ እና ትርፍን
አብዝቶ መፈለግ በችግርነት ተነስተዋል።
በጥራት ላይ የሚታዩ ችግሮችን ለመከላከል ከማሕንዲሶች፣ ከጸረ ሙስና፣ ከፖሊስ፣ ከፍትህ፣ ከኮንትራክተሮችና ከቴክኒክና ሙያ
ኢንተርፕራይዝ የተካተቱበት ቡድን ተዋቅሮ ክትትል እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
መሬት ከሦስተኛ ወገን አለመጽዳት፣ የስልክ እና መብራት ኃይል ፖሎች በወቅቱ ባለመነሳት ምክንያት ከዚህ በፊት መጠናቀቅ
የነበረባቸው መሠረተ ልማቶች ቢዘገዩም አሁን ባለው ፍጥነት ማከናወን ከተቻለ በግንቦት 2013 ዓ.ም ላይ ማጠናቀቅ
እንደሚቻል አቶ ዮርዳኖስ ገልጸዋል።
ዘጋቢ፦ ዳግማዊ ተሠራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በፌስቡክ https://bit.ly/2UwIpCw
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m

Previous article‹‹ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በህወሓት ደጋፊዎች ሀሰተኛ መረጃ በመታለል በኢትዮጵያ ላይ ያልተገባ ጫና ከማድረግ መቆጠብ አለበት›› በስዊዘርላንድ ጄኔቫ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን
Next article“ላለፉት ሦስት ዓመታት በተካሄደ የፖለቲካ ሪፎርም አሁን ላይ ራሳቸውን የቻሉ ገለልተኛ ተቋማትን ለመመስረት አስችሏል” በዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈሪ መለሰ