ባለፉት ስድስት ወራት ከ144 ሺህ በላይ ዜጎች የንፁህ መጠጥ ውኃ ተጠቃሚ መሆናቸውን የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አገኘሁ ተሻገር ተናገሩ፡፡

77
ባለፉት ስድስት ወራት ከ144 ሺህ በላይ ዜጎች የንፁህ መጠጥ ውኃ ተጠቃሚ መሆናቸውን የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አገኘሁ ተሻገር ተናገሩ፡፡
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 02/2013 ዓ.ም (አብመድ) በ2013 በጀት ዓመት ትኩረት ከተሰጠባቸው የመሰረተ ልማት ተቋማት አንዱ የንፁህ መጠጥ ውኃ አቅርቦትን ማሳደግ እንደሆነ ነው ርእሰ መሥተዳድሩ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት ያወታወቁት፡፡
ይህን ለማሳካት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በማፈላለግ በገጠርና በከተማ የተለያዩ የውኃ ተቋማት ግንባታ ተካሂዷል ብለዋል፡፡ በገጠር አነስተኛ የቧንቧ ዝርጋት ሥራዎችን በመሥራት 81 ሺህ 202 ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ ገልጸዋል፡፡ ሽፋኑንም በ2012 ዓ.ም ከነበረው ወደ 68 በመቶ ማሳደግ ተችሏል ብለዋል፡፡
በከተማ 63 ሺህ የኅብረተሰብ ክፍሎችን የንፁህ መጠጥ ውኃ ተጠቃሚ በማድረግ ሽፋኑን በ2012 ዓ.ም ከነበረው ወደ 65 ነጥብ 16 በመቶ ማሳደግ ተችሏል፡፡ በአጠቃላይ በገጠርና በከተማ 144 ሺህ 202 የኅብረተሠብ ክፍሎችን ተጠቃሚ በማድረግ በ2013 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ የነበረውን 66 ነጥብ 8 በመቶ ወደ 67 ነጥብ 61 በመቶ ከፍ ማድረግ ተችሏል ብለዋል፡፡
ርእሰ መሥተዳድሩ የመስኖ ፕሮጀክቶችን ማሳደግ ለምርትና ምርታማነት ማደግ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ በመሆኑ ጥናትና ዲዛይን ላይ የተመሰረተ የመስኖ አውታር ዝርጋታዎች እየተካሄዱ ይገኛሉ ብለዋል፡፡
እንደ ርእሰ መሥተዳድሩ ሪፖርት በግማሽ በጀት ዓመቱ አሳታፊ የግንባታ ሥራዎችን በመሥራት፣ ዲዛይንና ጥናት በማካሄድ ኅብረተሠቡን በዘመናዊ መስኖ ተጠቃሚ ለማድረግ ጥረት ሲደረግ ነበር፡፡ 1 ሺህ 400 ሄክታር የሚያለሙ የስድስት ነባር ፕሮጀክቶችን ጥናትና ዲዛይን ሥራ በማከናወን እስከ 2012 ዓ.ም ከነበረው 28 ነጥብ 5 በመቶ ወደ 43 ነጥብ 5 በመቶ በማድረስ የእቅዱን 34 ነጥብ 9 በመቶ ማጠናቀቅ ተችሏል ብለዋል፡፡
ርእሰ መሥተዳድሩ 9 ሺህ 683 ሄክታር መሬት የሚያለሙ 17 አዲስ ፕሮጀክቶችን የጥናትና ዲዛይን ሥራ በመሥራት የእቅዱን 29 ነጥብ 12 በመቶ ለማከናወን እንደተቻለ አስታውቀዋል፡፡ በ2013 ዓ.ም የመጀመሪያ ስድስት ወራት 100 ሄክታር የሚያለማ አንድ የመስኖ ፕሮጀክት ዲዛይን ሥራ እና 448 ሄክታር የሚያለሙ ሦስት ፕሮጀክቶች መጠናቀቃቸውንም በሪፖርታቸው አብራርተዋል፡፡
እንደ ርእሰ መሥተዳደሩ ሪፖርት ነባር ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ የነበረው እንቅስቃሴ የተሻለ ሆኖ ተገምግሟል፡፡ በግንባታ ዘርፍ የታቀዱ ፕሮጀክቶችን ማጠናቀቅ ባይቻልም ነባር ፕሮጀክቶችን በመጠገን የተጀመረው እንቅስቃሴ አበረታች ነበር ብለዋል፡፡ ይሁን እንጅ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ መጠናቀቅ የሚገባቸው የጥናትና የዲዛይን ሥራዎች፣ የነባር ፕሮጀክቶች ግንባታ ድጋፍና ክትትል በማድረግ ረገድ ውስንነቶች መኖራቸውን ጠቅሰዋል፡፡
በመሆኑም በቀጣይ ነባርና አዲስ ፕሮጀክቶችን ግንባታ እና ጥገና ሥራዎች በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ ማጠናቀቅ የሚያስችል የክትትልና የቁጥጥር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አቶ አገኘሁ አስታውቀዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ትርንጎ ይፍሩ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous articleባለፉት ስድስት ወራት ከልማት ድርጅቶች ምርትና አገልግሎት ሽያጭ 158 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ተሰበሰበ።
Next articleየዓድዋ ተጓዦች የመዝጊያ መርኃ ግብር በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው።