“የራሴ ጥረት፣ የመምህራንና የወላጆቸ ድጋፍ ውጤታማ አድርጎኛል” በእንጅባራ ዩኒቨርስቲ የከፍተኛ ማዕረግ ተመራቂ

191
“የራሴ ጥረት፣ የመምህራንና የወላጆቸ ድጋፍ ውጤታማ አድርጎኛል” በእንጅባራ ዩኒቨርስቲ የከፍተኛ ማዕረግ ተመራቂ
ባሕር ዳር ፡ ጥር 15/2013 ዓ.ም (አብመድ) ጠንክሮ በመሥራት ውጤት ማስመዝገብ እንደሚቻል ዛሬ በእንጅባራ ዩኒቨርስቲ በከፍተኛ ማዕረግ የተመረቀው መኳንንት ይርሳው ተናግሯል።
እንጅባራ ዩኒቪርስቲ ለመጀመሪያ ጊዜ ያሰለጠናቸውን 957 ተማሪዎችን ዛሬ አስመርቋል።
ካስመረቃቸው ተማሪዎችም መኳንንት ይርሳው የከፍተኛ ማዕረግ ተሸላሚ ሆኗል።
ጠንክሮ በማንበቡ ዓላማውን ማሳካቱንም የከፍተኛ ማዕረግ ተሸላሚው ተናግሯል።
የእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ ያስተማራቸውን የበኩር ልጆችን ሲያስመርቅ ተመራቂ መኳንንት ይርሳው በግብርና ኮሌጅ የተፈጥሮ አያያዝ ትምህርት ክፍል ከተሰጠው 44 የትምህርት ዓይነቶች 42 ቱን “A+” እና ሁለቱን ደግሞ “A ” ብቻ በማምጣት በ 4 ነጥብ የዩኒቨርስቲው የከፍተኛ ማዕረግ ተሸላሚ በመሆን ዋንጫ ተበርክቶለታል።
ተማሪ መኳንንት በዳንግላ ወረዳ ጊሳ ቀበሌ የሚኖሩ አርሶ አደር ወላጆቹ ወደ ዩኒቨርስቲ ሲገባ ከፍተኛ ውጤት በማምጣት እንዲመረቅ ይፈልጉ እንደነበር ተናግሯል። የወላጆቹንም ፍላጎት በሚገባ መፈፀም መቻሉንም ነግሮናል።
“ፈተናዎችን አልፈህ ሰርተህ ውጤታማ ስትሆን እጅግ ትኮራለህ” ያለው ተመራቂዉ መኳንንት ያቀደውን ውጤት ለማሳካት በዩኒቨርስቲ ቆይታው ለትምህርቱ ልዩ ትኩረት በመስጠት ያነብ እንደነበር አስረድቷል።
ጊዜውን በአግባቡ በመጠቀም ባስመዘገበው ውጤትም ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን እጅ የከፍተኛ ማዕረግ ተሸላሚ ዋንጫን መቀበል መቻሉ እጅግ እንዳስደሰተው ተናግሯል።
ተማሪ መኳንንት ከህፃንነቱ ጀምሮ ትምህርቱን ሲከታተል በከፍተኛ ውጤት እንዳጠናቀቀ አስረድቷል፣ በዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ ውጤት በማምጣት መድገም በመቻሉም መደሰቱን ገልጿል።
“ጠንክሬ በማንበብ ዓላማየን አሳክቻለሁ” ያለው መኳንንት ዩኒቨርሲቲው አዲስ በመሆኑ የቤተ መጻሕፍት እና ሌሎች ችግሮች የነበሩት ቢሆንም ከፍተኛ ውጤት እንዲያስመዘግብ የዩኒቨርስቲው መምህራን፣ ወላጆቹ እና የክፍል ጓደኞቹ ድጋፍ እንዳደረጉለት ተናግሯል።
ሌሎች ተማሪዎችም ጠቃሚ ካልሆኑ ነገሮች ራሳቸውን በማራቅ፣ ትምህርታቸውን ብቻ በመከታተል ለተሰለፉበት ዓላማ ሙሉ ትኩረት በመስጠት ውጤታማ በመሆን ራሳቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውን እና ሀገርን መጥቀም እንዳለባቸው መክሯል። በተለይም የጊዜ አጠቃቀማችን በእቅድ ሊመሩ ይገባል ብሏል።
ዘጋቢ:- አዳሙ ሽባባው – ከእንጅባራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous article‹‹የኢትዮጵያን አፈር ጭረው፣ ልጅ አሳድገው፣ ተምሮ ሀገርና ቤተሰብ ይቀይርልናል የሚሉ ዜጎች በገዛ መሬታቸው ላይ መጤ ተብለው ሲገደሉ ሲሳደዱ፣ መስማትና ማዬት ያማል›› ታማኝ በየነ
Next articleጋዜጠኛ ፍስሃ ተገኝ በሰሜን ወሎ ዞን ግዳን ወረዳ ለሚገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎች ያሰባሰበውን የ450 ሽህ ብር ድጋፍ ገቢ አደረገ፡፡