
ህወሓት ባለፉት ዓመታት የዘራውን ጥላቻ በማስተካከል የአማራና የትግራይ ህዝቦች የቀደመ አብሮነትን ማስቀጠል እንደሚገባ የጠለምት ወረዳ ነዋሪዎች ተናገሩ።
ባሕር ዳር፡ ጥር 13/2013 ዓ.ም (አብመድ) ህወሓት በሰበከው “የጨቋኝ ተጨቋኝ” የሀሰት ትርክት አብረው ለዘመናት በኖሩ የአማራና የትግራይ ህዝቦች መካከል አለመተማመን መፈጠሩን ነው ነዋሪዎች ያስረዱት።
ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ከፍያለው ኃይሉ እንደገለጹት የአማራና የትግራይ ህዝቦች አብሮነት የሰላሳ ዓመታት ታሪክ ሳይሆን ብዙ ሺህ ዓመታትን የዘለቀ ነው። በተለይም ደግሞ የጠለምት ወረዳ ለትግራይ ህዝብ ካለው ቅርበት የአማራና የትግራይ ህዝቦች የባህል፣ የቋንቋና የእምነት ትስስሩ የጠነከረ ነው ብለዋል። ይህንን ግንኙነት አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሚሰሩም አቶ ከፍያለው ገልጸዋል።
ወጣቱም የማንም የፖለቲካ መጠቀሚያ ከመሆን መታቀብና ህዝባዊ አንድነትን የሚጎዱ አካሄዶችን ሊታገል እንደሚገባ መክረዋል።
ወጣት ሀብታሙ ይርጋ ባለፉት ዓመታት ህወሓት በዘራው ጥላቻ የህዝቦች በጋራ አብሮ የመኖር እሴት መሸርሸሩን ነግሮናል። የህዝቦች ማንነት ለቡድኖች የጥቅም ማስፈጸሚያ መሣሪያ ሳይሆን የጥንቱን አብሮ የመኖር ባህል ማጠናከሪያ መሆን እንደሚገባ ነው ያስረዳን።
አቶ ንጉሴ ገ/ዋሕድ የተባሉ አስተያየት ሰጭ ደግሞ ባለፉት ዓመታት ህወሓት በሠራው ሥራ በህዝቦች መካከል አለመተማመን ተፈጥሯል ብለዋል።
ነዋሪዎቹ ህወሓት ባለፉት ዓመታት የዘራውን ጥላቻ በማስተካከል የአማራና የትግራይ ህዝብን የቀደመ አብሮነት ማስቀጠል እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
የህወሃት ቡድን በሀገር መከላከያ ከተወገደ በኋላ የተሻለ ለውጥ ቢታይም ችግሩን ሙሉ ለሙሉ ለመፍታት የህዝብ ለህዝብ ትስስርን የሚያጠናክሩ ሥራዎችን መንግሥት እና የእምነት ተቋማት ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ እንደሚገባም ነዋሪዎች ተናግረዋል።
ዘጋቢ፡- ዳግማዊ ተሠራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በፌስቡክ https://bit.ly/2UwIpCw
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ