
በአማራ ክልል በ 2013 ዓ.ም ከ4 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ሥራ እንደሚሳተፉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡
ባሕር ዳር፡ ጥር 01/2013 ዓ.ም (አብመድ) የዘንድሮዉ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ንቅናቄ በክልሉ ከጥር 4/2013 ዓ.ም ጀምሮ በይፋ እንደሚጀመርም ቢሮዉ አስታውቋል።
በአማራ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ሥራ በተደራጀና በንቅናቄ መልማት የጀመረዉ በ2003 ዓ.ም ነው። ከንቅናቄው በፊት የክልሉ የደን ሽፋን 6 ነጥብ 5 በመቶ ነበር፤ እስካሁን በተሠራዉ ሥራም የክልሉ የደን ሽፋን ወደ 14 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማለት እንደቻለ በክልሉ ግብርና ቢሮ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ አጠቃቀም ተወካይ ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት አስረድተዋል።
የደን ሽፋኑን ለማሳደግ የአሠራር ለውጥ መቀየሱን ተናግረዋል። በተለይ በ2008 ዓ.ም እና በ2009 ዓ.ም የሚተከሉ ችግኞች ባለቤት እንዲኖራቸው መደረጉ የደን ሽፋን ሥራዉ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ ማስቻሉን አቶ እስመለዓለም አብራርተዋል።
የክልሉ የደን ሽፋን ከፍ ማለቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ አይነተኛ ሚና መጫወቱን ያስረዱት ተወካይ ዳይሬክተሩ ቁጥራቸው ቀላል የማይባል አርሶ አደሮች ቋሚ የሆኑ ችግኞችን በመትከል ሕይወታቸዉን መለወጥ እንደቻሉ ገልጸዋል።
በክልሉ በተከታታይ ለአሥርት ዓመታት በተሠራዉ ሥነ አካላዊና ሥነ ሕይወታዊ ሥራም በዋነኝነት ከ21 ሺህ ተፋሰሶች ውስጥ 7 ሺህ ተፋሰሶች በዘለቄታዊ ሃብት እንዲያመነጩ መደረጉን ተወካይ ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።
የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ሥራዉ ከዘመቻ ሥራ ወጥቶ እንዲሠራም የአደረጃጀት ለውጥ መደረጉን አስረድተዋል። “ካሁን በፊት አሠራርና ዕቅድ ከክልሉ ነበር አስከ ቀበሌ ድረስ የሚወርደው ይህ አካሄድ ችግሮችን ለይቶ ሊቀርፍ ባለመቻሉና ሥራን ማቀላጠፍ ባለመቻሉ አደረጃጀቱ ሥራዉ በሚገኝበት (ከቀበሌ) መነሻ በማድረግ ወደ ክልል እንዲወርድ ተደርጓል” ብለዋል።
በክልሉ በዘንድሮ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ንቅናቄ 328 ሺህ ሄክታር በላይ እንደሚለማ ያስረዱት አቶ እስመለዓለም ሥራዉን ለማሳካት 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሕዝብ እንደሚሳተፍበት አስታውቀዋል። ለሥራውም ከ8 ሽህ 300 በላይ ተፋሰሶች መለየታቸውም ታውቋል፡፡
በክልሉ የ2013 ዓ.ም የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ንቅናቄ በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ላይ አርማጭሆ ወረዳ ጥር 4/2013 ዓ.ም በይፋ የሚጀመር ሲሆን ለሥራዉ ስኬታማነት ሕዝቡ፣ ባለሙያዉና በየደረጃዉ የሚገኙ የሥራ ኀላፊዎች ርብርብ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።
ዘጋቢ:- ብሩክ ተሾመ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ