የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በ40 የተለያዩ ቦታዎች በደረሰ ጥቃት የ123 ሰዎች ሕይወት ማለፉንና በ500 ሰዎች ላይ የአካል ጉዳት መድረሱን ኢሰመኮ ይፋ አደረገ፡፡

182
የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በ40 የተለያዩ ቦታዎች በደረሰ ጥቃት የ123 ሰዎች ሕይወት ማለፉንና በ500 ሰዎች ላይ የአካል ጉዳት መድረሱን ኢሰመኮ ይፋ አደረገ፡፡
ባሕር ዳር፡ ታኅሣሥ 23/2013 ዓ.ም (አብመድ) የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በተከሰተ የፀጥታ መደፍረስ የተሳተፉ ሰዎችና ቡድኖች በሲቪል ሰዎች ላይ ያደረሷቸው ጥቃቶች በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ባሕርያትን የሚያሟሉ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን አስታውቋል።
ኮሚሽኑ በዛሬው እለት ባወጣው መግለጫ እነዳስታወቀው ኦሮሚያ ክልል የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ተከስቷል፤ አጥፊዎቹም ሕግ ፊት መቅረብ አለባቸው ሲል ነው ያስታወቀው።
“የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል ልዩ ልዩ አካባቢዎች በተከሰተ የፀጥታ መደፍረስ የተሳተፉ ሰዎችና ቡድኖች በሲቪል ሰዎች ላይ ያደረሷቸው ጥቃቶች በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ባሕርያትን የሚያሟሉ መሆናቸውን በምርመራ ሪፖርቱ ተመላክቷል።
ኢሰመኮ ከሰኔ 22/2012 ዓ.ም ጀምሮ በነበሩ ሦስት ተከታታይ ቀናት በኦሮሚያ ክልል የተከሰተውን የፀጥታ መደፍረስና የሰብአዊ መብቶች ጥሰት የባለሞያ ቡድኖቹን ወደ 40 የክልሉ አካባቢዎች የላከ ሲሆን፣ የምርመራውን ግኝቶች ታኅሣሥ 23/2013 ዓ.ም ይፋ አድርጓል።
በ59 ገጽ ሪፖርቱ እንደተመለከተው፣ በዚህ መጠነ ሰፊ ጥቃት የተሳተፉት ብዙ ቁጥር ያላቸው እና ከቦታ ቦታ በቡድን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሰዎች ሲሆኑ፤ በጩቤ፣ በድንጋይ፣ በእሳት፣ በኤሌክትሪክ ገመድ፣ በዱላ፣ በዶማ፣ በገጀራ እና በመጥረቢያ ተጠቅመው ሰዎችን ደብድበዋል፣ የአካል ጉዳት አድርሰዋል፣ ፍጹም ግፍና ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ በማሰቃየት እና በማረድ ጭምር ሰዎችን ገድለዋል።
በጥቃቶቹ የ123 ሰዎች ሕይወት አልፏል፣ 500 ሰዎች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተፈናቅለዋል።
በአብዛኛው በቡድን የተደራጁ ሰዎች ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ፣ በብሔርና በሃይማኖታቸው ተለይተው የተመረጡ ሲቪል ሰዎችን፣ ቢያንስ በ40 የተለያዩ ቦታዎች በተስፋፋና ለሦስት ቀናት በቆየ ሁከት ማጥቃታቸው፣ በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል እንደሚያደርገው ኮሚሽኑ አብራርቷል።
ጥቃቱም በአብዛኛው በአማራ ብሔር ተወላጆችና በኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኞች ላይ ያነጣጠረ እንደነበር ሪፖርቱ ገልጿል።
ምንም እንኳን የፀጥታ ኃይሉ በየቦታው የገጠመውን መጠነ ሰፊ የፀጥታ መደፍረስ ችግር እና የፀጥታ አባሎቹንም የሕይወት መስዋዕትነት በሚጠይቅ ሁኔታ በመሰማራታቸው ኃላፊነታቸው እጅግ ፈታኝ የነበረ መሆኑን መገንዘብ ቢቻልም፤ በተወሰኑ ቦታዎች የኃይል አጠቃቀም ተመጣጣኝነት ከፍተኛ ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑን ኮሚሽኑ በሪፖርቱ አክሎ ገልጿል።
በአንዳንድ አካባቢዎች የፀጥታ ኃይሉ በወሰደው ያልተመጣጠነ እርምጃ፣ ሰልፍ ውስጥ ያልነበሩ፥ በመንገድ ወይም በቤታቸው በር ላይ የተገደሉ፣ ለማሸማገል ጣልቃ የገቡ የአገር ሽማግሌዎችን እና የአዕምሮ ህመምተኛ ጭምር እንዲሞቱ ምክንያት ሆኗል ብሏል።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል በቀለ “በኢትዮጵያ የሚታየው የግፍና የጭካኔ ወንጀሎች መደጋገም፣ የችግሩን ስር መሰረት ለመፍታት የሚያስችል የተሟላ ብሔራዊ የግፍና ጭካኔ ወንጀል መከላከያ ስትራቴጂ ነድፎ በአፋጣኝ በስራ ላይ ማዋል እንደሚገባ የሚያሳይ መሆኑን” ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡- ዘመኑ ታደለ- ከአዲስ አበባ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በፌስቡክ https://bit.ly/2UwIpCw
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
Previous article“የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ተከስቷል” ኢሰመኮ
Next articleማንነትን መሰረት ያደረገ ምጣኔ ሀብታዊ መድሎ እና መገለል – በጠለምት ጥቁር ውኃ ከተማ