
ባሕር ዳር፡ ኅዳር 05/2013 ዓ.ም (አብመድ) ግብረኃይሉ በዛሬው ዕለት በብሄራዊ ቲአትር ከአርቲስቶች ጋር የውይይት መርሃ ግብር አካሂዷል፡፡
“የኪነጥበብ ሙያተኛ ሃብቱ ሰው ነው፤ሃገርና ህዝብን ከየትኛውም ጥቃት ለመጠበቅ በጽኑ እንሰራለን፤ለህዝቡም እንታገላለን” ብሏል የኪነጥበብ ግብረኃይሉ፡፡
በሰሜን ዕዝ የመከላከያ ሰራዊት ላይ የተፈጸመው ጥቃት ከባዕድ ሃገር በገባ ጠላት እንኳን ያልተፈጸመ ግፍ ነው ያሉት የኪነጥበብ ሙያተኞቹ ሁሉም ይህን ለመመከት በትብብር የሚነሳበት ወቅት ነውም ብለዋል።
የመከላከያ ሰራዊት ለኪነጥበብ ዘርፉ ያበረከተው አስተዋጽዖ ከፍተኛ ነው ያሉት አርቲስቶቹ አሁን ላይ በሃገሪቱ ያሉ ታላላቅ የኪነጥበብ ሙያተኞች የመከላከያ ሰራዊት ፍሬዎች መሆናቸውንም አንስተዋል፡፡
ሃገር ካላት ትልልቅ ምሰሶዎች አንዱ የመከላከያ ሰራዊት ነው፤ መከላከያ ሲነካ ሁሉም ተነቃንቋል፤ ተሰምቶናልም ብለዋል።
መከላከያ ሰራዊት አሁን ላይ እያደረገ ላለው የህግ ማስከበር ተግባር አርቲስቶች አጋርነታቸውን ለመግለጽ የገንዘብ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር እንደሚያዘጋጁ ተመልክቷል፡፡
ለሃገር መከላከያ በሚደረገው ድጋፍ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንም አጋርነታቸውን እንዲያሳዩም ተጠይቋል፡፡
ዘጋቢ፡- እንዳልካቸው አባቡ – ከአዲስ አበባ