
ባሕር ዳር፡ ኅዳር 04/2013 ዓ.ም (አብመድ) በትግራይ ክልል እየተካሄደ ያለው ሕግ የማስከበር ሥራ ዒላማ ያደረገው ሕግ የጣሱ ግለሰቦችን እንጂ ሠላማዊ ዜጎችን አለመሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ላደረጉ አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ገልጸዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ላደረጉ አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ገለፃ አድርገዋል።
በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል እየተከናወነ ስለሚገኘው የሕግ የበላይነትን የማስከበር ሥራም አብራርተውላቸዋል።
ሕግ የማስከበር ሥራው ዒላማ ያደረገው ሕግ የጣሱ ግለሰቦችን እንጂ ሠላማዊ ዜጎችን አለመሆኑንም ገልፀዋል።
በኢትዮጵያ የመጣውን ለውጥ ተከትሎ ሲሰሩ የቆዩ ዘርፈ ብዙ የሪፎርም ተግባራትን የዘረዘሩት አቶ ደመቀ፤ አገሪቷን ወደ ሠላም፣ ዴሞክራሲና ብልጽግና ለማሻገር እንቅስቃሴ ላይ እንደሆነም ጠቅሰዋል።
ይሁንና የለውጡን ሂደት ለማበላሸት እየተንቀሳቀሰ ያለው የህወሓት ቡድን ባለፉት ሁለት ዓመታት በኢትዮጵያ ሠላም፣ ዴሞክራሲና ብልጽግና እንዳይመጣ የተለያዩ እኩይ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን አውስተዋል።
በሀገሪቷ የተለያዩ አካባቢዎች ግጭቶች እንዲፈጠሩ በማድረግ ሠላማዊ ዜጎች ላይ ጉዳት እንዲደርስና ሀገሪቷ እንዳትረጋጋ እኩይ ዓላማ ካነገቡ ሀይሎች ጋር ሲሰራ መቆየቱንም ገልፀዋል።
መንግስት ይህን ሁኔታ ለመፍታት ላለፉት ሁለት ዓመታት ያሳየው ከልክ ያለፈ ትዕግስት ለሠላም ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያል ነው ያሉት አቶ ደመቀ፤ ይሁን እንጂ ይህ ቡድን የአፍሪካ ኩራት በሆነው የመከላከያ ሠራዊት ላይ ጥቃት አድርሷል ብለዋል።
ዘራፊው የህወሓት ቡድን በሠላማዊ ዜጎች ላይ ጉዳት እያደረሰ ስለመሆኑም ተናግረዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን የሕግ ማስከበር ሥራ አጠር ባለ ጊዜ ለማከናወን እየተሰራ ነውም ብለዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲም ሕግ የማስከበር ሥራው ዒላማ ያደረገው ሕግ የጣሱ ግለሰቦችን እንጂ ሠላማዊ ዜጎችን አለመሆኑን ለአምባሳደሮችና ዲፕሎማቶቹ ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለው ሕግ የማስከበር ሥራ እንጂ የእርስ በእርስ ጦርነት እንዳልሆነ ለአምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ተገልጿል፤ ይህ ስራ አጠር ባለ ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል ሲል የዘገበው ኢዜአ ነው።
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m