
የአማራ ክልል የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት የነበሩት ሼህ አህመድ ሙሐመድ አረፉ፡፡ ሼህ አህመድ ሙሀመድ በሰሜን ወሎ ዞን ሀብሩ ወረዳ ከረም በተባለ ቦታ ከእናታቸው ሃሊማ ሼሁ እና ከአባታቸው ሼህ ሙሀመድ ሰይድ በ1948 ዓ.ም ተወለዱ፡፡
ሼህ አህመድ በሀገር ውስጥ ከረንና እና ከረም ቀርተዋል፡፡ በሳዑዲ አረቢያ ደግሞ አረበኛ፣ ተውሂድ እና ሀዲስን ተምረዋል፡፡ በ1985 ዓ.ም ከሳዑዲ አረቢያ ተመልሰው ከወልዲያ ከተማ የሰላም መስጅድ ትምህርት ቤት በማስተማር እና በልዩ ልዩ ሐይማኖታዊ አግልግሎቶች ተሳትፈዋል፡፡
ከ2005 ዓ.ም ጅምሮ ደግሞ የአማራ ክልል የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው አገልገለዋል፡፡ ሼህ አህመድ ሙሐመድ መስጊዶችን በማሰራት እና በልዩ ልዩ ማህበራዊ አግልግሎታቸው በመልካም ስነ ምግባር የሚታወቁ ነበሩ፡፡
የሦስት ወንድ ልጆች እና የአምስት ሴት ልጆች አባት ሼህ አህመድ ሙሐመድ በተወለዱ በ65 ዓመታቸው ዛሬ ህዳር 4 ቀን 2013 ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት በትውልድ ስፍራቸው ከረም መስጅድ ስርዓተ ቀብራቸው ተፈፅሟል።
የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት ለቤተሰቦቻቸው እና ለወዳጅ ዘመድ መጽናናትን ይመኛል፡፡
ዘጋቢ፡- ባለ ዓለምየ- ከሀብሩ