
ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም (አብመድ) የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋኪ ማህማት በኢትዮጵያ በንፁሃን ላይ የተፈፀመውን ግድያ አውግዘው፤ የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን ገልፀዋል፡፡
ሊቀ መንበሩ ለተጎጂ ቤተሰቦች መፅናናትን እመኛለሁ ካሉ በኋላ መንግስት አጥፊዎችን ለህግ እንዲያቀርብ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ አካታች ውይይት ያስፈልጋል፤ የአፍሪካ ህብረትም አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡
በሃገሪቱ ብሄር ተኮር ጥቃት እየተበራከተ መጥቷል ያሉት ሊቀ መንበሩ ሁሉም ባለ ድርሻ አካላት ወደ ሰከነ ፖለቲካዊ ውይይት መምጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ ቁልፍ በሆኑ ጉዳዮች ላይም ሐገራዊ መግባባት ላይ እንዲደረስ ጠይቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ አለመረጋጋት ለሃገሪቱ ብቻ ሳይሆን ለቀጣናው አለመረጋጋት ምክንያት ይሆናልም ነው ያሉት ሊቀ መንበር ሙሳ ፋኪ፡፡
በኢትዮጵያ ለተጀመረው ሃገራዊ ለውጥ እና ሰላም አፍሪካ ህብረት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉም ሊቀ መንበሩ መናገራቸውን ከአፍሪካ ህብረት ይፋዊ ገፅ የተገኘ መረጃ ያመላክታል፡፡
በታዘብ አራጋው