
ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም (አብመድ) በምዕራብ ወለጋ ዞን በጉሊሶ ወረዳ ዘር ተኮር ጥቃት ደርሷል፡፡ አብመድ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች እንዳሉት በተፈፀመው ግድያ ህይወታቸው ያለፉ ሰዎችን አስክሬን በክብር እያሳረፉ ነው፤ የቆሰሉትንም ወደ ህክምና በማድረስ ላይ ናቸው፤ ለህክምና ከተወሰዱት 12 ሰዎች መካከል ደግሞ የሁለቱ ሰዎች ሕይወት ማለፉንም ነግረውናል፡፡
“በጥቃቱ ምክንያት ምንም ምግብ ያላገኙ ህፃናት ለርሃብ መጋለጣቸውን በመጥቀስም አስቸኳይ ድጋፍ ያስፈልጋል” ብለዋል ነዋሪዎቹ፡፡ መንግሥት ችግሩን ተረድቶ ፈጣን ምላሽ እንዲሰጥም ጠይቀዋል፡፡
ወደ አካባቢው የኦሮሚያ ልዩ ኃይል ቢገባም መኖሪያውን ጫካ ያደረገው ኦነግ ሸኔ ላይ ምንም እርምጃ እየወሰደ አይደለም፤ በዚህም ዛሬ ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም ጠዋት ንብረት አቃጥለው መሄዳቸውን ተናግረዋል፡፡
በአካባቢው የፀጥታ ሃይል ቢገባም አልተረጋጋንም፤ መንግስት ቢደርስም አስቸኳይ ምላሽ መስጠት ሲገባው ጉዳዩን ወደ ውይይት እየወሰደው እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
በቀበሌው ሁሉም ምግብ ቤቶች ዝግ ናቸው፤ ሀብት ንብረትም ወድሟል ወደ አካባቢው ለመመለስ የሚያስችል ቅድመ ሁኔታም የለም ነው ያሉት ነዋሪዎቹ፡፡