በባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር በ23 ሚሊዮን ብር የተገነቡ የትምህርት ቤቶች ማስፋፊያ ግንባታዎች ተመረቁ።

334

ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 07/2013 ዓ.ም (አብመድ) በባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር እና በበጎ ፈቃደኛ ባለሃብት የተገነቡ የማስፋፊያ ግንባታዎች ለ2013 የትምህርት ዘመን ዝግጁ ሆነዋል። በፕሮግራሙ ላይ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ይልቃል ከፋለ (ዶ.ር)ን ጨምሮ የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

የማስፋፊያ ግንባታዎቹ 23 ሚሊዮን ብር ወጭ እንደተደረገባቸው በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ ተገልጿል፡፡ የመማሪያ ክፍሎች፣ የአስተዳደር ሕንጻዎች እና ቤተ ሙከራ ሕንጻዎች ይገኙበታል።

የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ተሻገር አዳሙ በከተማ አስተዳደሩ የሚታየውን የመማሪያ ክፍል ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ የተማሪ ቁጥር ባለባቸው ትምህርት ቤቶች ተጨማሪ ክፍሎች በግንባታ ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ማኅበረሰቡ እና ባለሃብቶችም ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል።

የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ይልቃል ከፋለ (ዶ.ር) በፕሮግራሙ ላይ ሕንጻ ብቻ መገንባት በቂ ስኬት አለመሆኑን አሳስበዋል፤ ተማሪዎች በስነ ምግባር የታነጹ እና ችግር ፈቺ እውቀት እንዲቀስሙ ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ርብርብ ሊያደርግ እንደሚገባ አሳስበዋል።

በዚህ ወቅት በክልሉ ካሉት ትምህርት ቤቶች 84 በመቶ ከደረጃ በታች መሆናቸውን ዶክተር ይልቃል ተናግረዋል፤ በትምህርት ቤቶች ገጽታ ግንባታ ባለሃብቶች እና ማኅበረሰቡ እንዲሳተፉም ጥሪ አቅርበዋል።

በ2013 የትምህርት ዘመንም ተማሪዎች የኮሮና መከላከያ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ በመጠቀም ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል። በባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር 41 አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እና 11 ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ይገኛሉ።

ዘጋቢ:- ዳግማዊ ተሰራ

ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m

Previous articleበሰሜን ወሎ ዞን በተከሰተው የበርሃ አምበጣ ለተጎዱ ወገኖች የሚደረግ ድጋፍ ህጋዊ የመንግስት አሰራርን ተከትሎ እንደሚካሄድ የዞን አስተዳደሩ አስታውቋል፤ግለሰቦች የድጋፍ ሒሳብ ደብተር በመክፈት የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ህጋዊነት እንደሌለውም ተጠቁሟል፡፡
Next articleበሕዝቦች መካከል ጥርጣሬ እንዲኖር የሚተጉ ኃይሎችን በጋራ መታገል እንደሚገባ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ገለጹ፡፡