በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ባቲ ወረዳ የተከሰተው የአንበጣ መንጋ አሁን ላይ በብሔረሰብ አስተዳደሩ አምስት ወረዳዎች ላይ እየተስፋፋ መሆኑ ተገለፀ፡፡

496

የአንበጣ መንጋዉም በአምስት ወረዳዎች በሚገኙ 46 ቀበሌዎችን የሸፈነ ሲሆን ከ7 ሺህ 200 ሄክታር በላይ ሰብል ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ታውቋል። በዚህም ከ12 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች የችግሩ ሰለባ መሆናቸዉን የብሔረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ያገኘነዉ መረጃ ያመለክታል፡፡

ለአብነትም በባቲ ወረዳ ብቻ በ15 ቀበሌዎች የሚገኝ ሰብል ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ መዉደሙን የብሔረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ኃላፊ እብሬ ከበደ ገልፀዋል፡፡
ጉዳቱንም ለመከላከል በባህላዊና በዘመናዊ መንገድ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የገለፁት የመምሪያ ኃላፊዉ በዚህ ተግባር ላይም የመንግሥት ሠራተኞች፣ ባለሀብቶች፣ እንዲሁም አርሶ አደሮች እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

አቶ እብሬ ከበደ አክለዉም አሁን ላይ በአንድ አዉሮፕላን የኬሚካል ርጭት እየተደረገ መሆኑን በመግለፅ ከችግሩ በከፍተኛ ሁኔታ መስፋፋት ጋር ተያይዞ ከ7 እስከ 10 አዉሮፕላን እንደሚያስፈልግ በባለሙያ የተጠና መሆኑን ገልፀዋል። የክልሉ ግብርና ቢሮና የፌዴራል የግብርና ሚኒስቴር ጉዳዩ ጊዜ የማይሰጥ መሆኑን ከግምት ዉስጥ በማስገባት በጋራ መፍትሔ ሊያበጁለት እንደሚገባም ጠይቀዋል፡፡

ዘጋቢ፦ ይማም ኢብራሂም -ከከሚሴ

Previous articleበጎርፍ አደጋ ለተፈናቀሉ ዜጎች 2 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ተደረገ፡፡
Next articleሐሰተኛ የብር ኖቶችን ለመከላከል በትኩረት እየሠራ መሆኑን የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡