የቻይናው ማዕድን (ሻንዢ) ኢነርጂ ግሩፕ በኢትዮጵያ የመሰማራት ፍላጎት እንዳለው ገለጸ።

115

ባሕር ዳር፡ ሰኔ 06/2015 ዓ.ም (አሚኮ) አምባሳደር ተፈራ ደርበው ከቻይና ማዕድን (ሻንዢ) ኢነርጂ ግሩፕ ሊቀመንበር ዣንግ ዢ ፔንግ ጋር በኢትዮጵያ በዘርፉ መዋዕለ ንዋይ ፈሰስ ማድረግ በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ተወያይተዋል።

በውይይቱ ወቅት አምባሳደሩ ኢትዮጵያ ቅድሚያ በሰጠቻቸው የኢንዱስትሪ ዘርፎች ስላለው ከፍተኛ የኢንቨስትመንት አቅም ለሊቀመንበሩ እና ለቡድናቸው ገለፃ አድርገዋል።

ባለፉት ተከታታይ ዓመታት ኢትዮጵያን ለውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ተወዳዳሪ እና ተፈላጊ ያደረጉ ውጤታማ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች መተግበራቸውንም ጠቅሰዋል።

አምባሳደሩ አክለውም በኢትዮጵያ በማዕድን ዘርፍ ለምን መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ እንዳለባቸውም አብራርተውላቸዋል።

የኩባንያው ሊቀመንበር ዣንግ ዢ ፔንግ በበኩላቸው ፥ የቻይና ማዕድን (ሻንዢ) ኢነርጂ ግሩፕ በቻይና ከፍተኛ ኢንቨስትመንት እና ገበያ ያለው የታወቀ የማዕድን እና ኢነርጂ ኩባንያ መሆኑን አስረድተዋል።

ኩባንያው በኢትዮጵያ ማዕድን ልማት ዘርፍ ላይ የመሰማራት ፍላጎት እንዳለው በመጥቀስም፥ ወደ ሥራ ለመግባት አስፈላጊውን አደረጃጀት እያሟላ ነው ማለታቸውን በቻይና የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል።

በቻይና የኢትዮጵያ ኤምባሲም የኩባንያውን በኢትዮጵያ የመሰማራት ፍላጎት ለማመቻቸት ዝግጁ መሆኑን አምባሳደር ተፈራ በዚህ ወቅት ገልጸዋል።

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!