ባሕር ዳር: ኅዳር 10/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የፓን አፍሪካ ፓርላማ አባላትና ቋሚ ኮሚቴዎች አዲስ አበባ ላይ የጋራ ስብሰባቸውን እያካሄዱ ነው፡፡ አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ በጉባዔው ላይ ባደረጉት መክፈቻ ንግግር÷ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አንድነት መመስረት የነበራት አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡ በቀጣይም የሚስተዋሉት ችግሮች ተቀርፈው የበለጸገች አፍሪካን እውን ለማድረግ ኢትዮጽያ የጸና አቋም አላት ብለዋል፡፡
የፓርላማ ዲፕሎማሲ የጋራ ችግሮቻችንን ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመው፣ የፓን አፍሪካ ፓርላማም የቁልፍ ችግሮች መፍቻ በመሆኑ ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡
አፍሪካ የሰው ዘር መገኛ፣ የጥንታዊ ሥልጣኔ ባለቤት እንዲሁም ከፍተኛ የመልማት አቅም ያላት በመኾኗ በአሕጉሪቱ እየተስተዋለ ላለው ችግር መፍሄ ማምጣት ከተቻለ የአፍሪካን ብልጽግና ማረጋገጥ እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡
በአፍሪካ አሕጉር እየተስተዋሉ ካሉት ችግሮች መካከል ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ ድህነት እና የእርስ በርስ ግጭት ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን አፈ-ጉባኤው ጠቅሰዋል፡፡ለእነዚህ ችግሮች መፍትሄ ለማምጣት ሁሉም የአፍሪካ ሀገራት በትብብር ሊሠሩ ይገባል ሲሉም ተናግረዋል።
የፓን አፍሪካ ፓርላማ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት አሸብር ወልደጊዮርጊስ (ዶ.ር) በአፍሪካ እየተባባሰ የመጣው ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር መፍትሔ ሊበጅለት እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!